ቀጥታ፡

አርሶ አደሩ የክረምት ዝናብና የእርጥበት እቀባን በመጠቀም ፈጥነው የሚደርሱ ሰብሎችን መዝራት አለበት

ደሴ፤ ሰኔ 25/2018 (ኢዜአ)፡-አርሶ አደሩ የክረምቱን ዝናብ እና የእርጥበት እቀባን በመጠቀም ፈጥነው የሚደርሱ ሰብሎችን ሊዘራ እንደሚገባ የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት የምስራቅ አማራ ማዕከል አስታወቀ።

ማዕከሉ የ2018 ዓ.ም ክረምት ወቅት የዝናብ ስርጭትን በማስመልከት መከናወን ባለባቸው ጉዳዮችና ጥንቃቄዎች ላይ በደሴ ከተማ ከባለድርሻ አካላት ጋር መክሯል።

በመድረኩ የምስራቅ አማራ ሚቲዎሮሎጂ አገልግሎት ማዕከል መሪ ሥራ አስፈጻሚ አቶ ይመር መሀመድ እንደገለጹት፣ የክረምት ዝናብ መደበኛና ከመደበኛ በታች እንደሚሆን የአየር ትንበያ መረጃዎች ያሳያሉ።


 

አርሶ አደሩ የክረምትን ዝናብ ውሀ በማሰባሰብ ለልማቱ መዋልና ፈጥነው የሚደርሱ ሰብሎችን መዝራት እንደሚጠበቅበት  ተናግረዋል።

ይህን የግብርና መረጃ ለአርሶ አደሩ ግንዛቤ ከመፍጠር ባለፈ ግብዓት  በወቅቱ በማቅረብ መደገፍ ያስፈልጋል ብለዋል።

በማዕከሉ የትንበያና ቅደመ ማስጠንቀቂያ ዴስክ ኃላፊ ወይዘሮ ሉባባ መሀመድ በበኩላቸው፣ በምስራቅ አማራ ቀጠና የ2018 ዓ.ም ክረምት ዝናብ  ቀድሞ ሊወጣ እንደሚችል ገልጸዋል።

ለዚህም የዘር ሥራውን ፈጥኖ መጀመርና የጎርፍ ውሃን አሰባስቦ እርጥበትን በማቀብ ለደረቃማ ቀናት መጠቀም እንደሚገባ አስገንዝበዋል።


 

ፈጥነው የሚደርሱና ድርቅ የሚቋቋሙ የሰብል ዝርያዎችን በመጠቀም ምርታማነትን ማሳደግ እንደሚገባም ገልጸዋል።

አርሶ አደሩም የግብርና ባለሙያዎችን ምክር በመተግበር ሰብሉን ከቅጽበታዊ ጎርፍ፣ በሽታና ተባይ መጠበቅ አለበት ብለዋል።

የክረምት ዝናብን በአግባቡ በመጠቀም፣ ውሃ በማሰባሰብ፣ ፈጥነው የሚደርሱ ሰብሎችን በመዝራት ምርታማነትን ለማሳደግ ቅደመ ዝግጅት መደረጉን የገለጹት ደግሞ በደቡብ ወሎ ዞን ግብርና መምሪያ የሰብል ልማት ባለሙያ አቶ ወንድይፍራው ጎቾ ናቸው።


 

በዞኑ የዝናብ እጥረት ሊከሰትባቸው የሚችሉ ወረዳዎች ተለይተው ፈጥኖ የሚደርስ ምርጥ ዘር እንዲቀርብ እየተደረገ ነው ብለዋል።

እንደ ባለሙያው ገለጻ በዞኑ 437 ሺህ ሄክታር መሬት በማልማት 16 ሚሊዮን ኩንታል ምርት ለማግኘት ዝግጅት ተደርጎ  ወደተግባር ተገብቷል።

የኦሮሞ ብሔረሰብ አስተዳደር ዞን ግብርና መምሪያ የሰብል ልማት ቡድን መሪ አቶ ደጀኔ ከበደ በበኩላቸው እንዳሉት፣ የትንበያውን ምክረ ሀሳብ በመውሰድ አርሶ አደሩ ሰብሉን ቀድሞ እንዲዘራ ተደርጓል። 


 

በዚህም በተያዘው የመኸር ወቅት ከሚለማው 58 ሺህ ሄክታር መሬት ከ27 ሺህ ሄክታር በላይ የሚሆነው በዘር መሸፈኑን ጠቁመው፣ ቀሪውን ፈጥኖ በሚደርሱ ሰብሎች ለመሸፈን ከአርሶ አደሩ ጋር በቅርበት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል።

በመድረኩ የምስራቅ አማራ ቀጠና ዞኖች የግብርና፣ ጤና፣ አደጋ መከላከልና ሌሎች ባለድርሻ አካላት አመራሮችና ባለሙያዎች ተሳትፈዋል።

 

 

 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም