ቀጥታ፡

ኢትዮጵያ የባሕር በር ብታገኝ የሚጠቀም እንጂ የሚጎዳ ሀገር እንደሌለ ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ተገንዝቧል

አዲስ አበባ፤ ሰኔ 25/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ታሪካዊ፣ ሕጋዊና መልክዓ ምድራዊ መሰረት ያለው የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ ዓለም አቀፍ ተቀባይነት ያለው ወሳኝ አጀንዳ መሆኑን ምሁራን ገለጹ።

ምሁራኑ ለኢዜአ እንዳሉት፤ የኢትዮጵያን የባሕር በር ባለቤትነት መብት ለማስከበር የሚከናወኑ ተግባራት ሳይንሳዊና ዲፕሎማሲያዊ መንገድን የተከተሉ ናቸው።

የሀገር ውስጥ ባንዳና የውጭ ባዕዳን ኃይሎች ኢትዮጵያ ላለፉት ሦስት አሥርት ዓመታት በላይ ከተፈጥሯዊና ታሪካዊ የባሕር በር ባለቤትነት ተነጥላ እንድትቆይ ማድረጋቸው ይታወሳል።

ከሀገራዊ ለውጡ ማግስት የመደመር መንግሥት የትውልድን የተዳፈነ ጉዳይ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ጥቅም አጀንዳ በማድረግ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄን ወደ ዓለም አቀፍ ቅቡልነት አሸጋግሯል።

በኢትዮጵያ ፐብሊክ ሰርቪስ ዩኒቨርሲቲ የዲፕሎማሲና ዓለም አቀፍ ግንኙነት መምህር እንዳለ ንጉሴ፤ የባሕር በር ባለቤትነት የሀገርን ሁለንተናዊ ሉዓላዊነት የሚያረጋግጥ የብሔራዊ ጥቅም ማዕከል ነው ብለዋል።

የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ ከታሪካዊ፣ መልክዓ ምድራዊና ሕጋዊ መሠረት ባሻገር ብሔራዊ ጥቅምንና አዳጊ የሀገርና የዜጋ ፍላጎትን ማዕከል ያደረገ ወሳኝ ጉዳይ መሆኑን አንስተዋል።

በዚህም ሕዝብና መንግሥት የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄን ምላሽ ለማስገኘት በውጤታማ የውጭ ግንኙነት ፖሊሲ በተደገፈ ሳይንሳዊ የዲፕሎማሲ መርህ ወደ ዓለም አቀፍ ቅቡልነት ማሸጋገራቸውን አስረድተዋል።

የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነትም ሀገርን ከተፈጥሯዊ ማንነቷ በማስታረቅ ቀጣናዊ ሰላምና ደኅንነትን ዕድገትና ብልፅግናን የሚያረጋግጥ ወሳኝ የትብብር ዕድል መሆኑን አስገንዝበዋል።

ኢትዮጵያ የባሕር በር ብታገኝ የሚጠቀም እንጂ የሚጎዳ ሀገር እንደሌለ ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ መገንዘቡንም ነው ያነሱት።

ኢትዮጵያ ጫናን በመቋቋም በዲፕሎማሲ ስኬት ሕዳሴ ግድብን ዕውን በማድረግ ቀጣናዊ የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ትስስርን በመፍጠር ተምሳሌታዊነቷን በተግባር እያስመሰከረች እንደምትገኝም ገልጸዋል።

ኢትዮጵያውያንም ሕዳሴን በትብብር እንዳሳኩት ሁሉ፤ አንድነትን በማጠናከር የትውልድ ጥያቄ የሆነውን የባሕር በር ባለቤትነት ለማስከበር በቁርጠኝነት ሊሰሩ እንደሚገባ ገልጸዋል።

በዩኒቲ ዩኒቨርሲቲ የሥነ-አመራርና ዓለም አቀፍ ግንኙነት መምህሩ ጌትዬ ትርፌ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ የባህር በር ያጣችው በውጭ ታሪካዊ ጠላቶችና በውስጥ ባንዳዎች ጥምር ሴራ ነው ብለዋል፡፡

ኢትዮጵያ ከባሕር በር ባለቤትነቷ እንድትርቅ የተፈጸመባት ኢ-ፍትሐዊ በደል ቀጣናውን የሽብርተኞች መፈንጫ በማድረግ የጋራ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን እያቀጨጨ መሆኑን ገልጸዋል።

በአሁኑ ወቅት የኢትዮጵያን የባሕር በር ባለቤትነት ብሔራዊ ጥቅምን የማስከበር የህልውና ጉዳይ ሆኖ መቅረቡም ቅቡልነት ያለው አጀንዳ መሆኑን ተናግረዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም