በኢትዮጵያ በቱሪዝም ልማትና ቅርስ ጥበቃ የተከናወኑ ተግባራት አስደናቂ ውጤት የተመዘገበባቸው ናቸው - ኢዜአ አማርኛ
በኢትዮጵያ በቱሪዝም ልማትና ቅርስ ጥበቃ የተከናወኑ ተግባራት አስደናቂ ውጤት የተመዘገበባቸው ናቸው
ወላይታ ሶዶ፤ ሰኔ 24/ 2018 (ኢዜአ):- በኢትዮጵያ ባለፉት ጥቂት ዓመታት በቱሪዝም ልማትና ቅርስ ጥበቃ ረገድ የተከናወኑ ተግባራት አስደናቂ ውጤት የተመዘገበባቸው መሆኑን ምሁራን ገለጹ።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) “ቱሪዝም አዲሱ የኢኮኖሚ ሞተር!” በሚል በሰጡት ማብራሪያ በዘርፉ ልማት የተከናወኑ ተግባራትንና የመጡ ውጤቶችን በስፋት አንስተዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማብራሪያቸው የብዝሃ የኢኮኖሚ አማራጮችን መሰረት አድርጎ በመስራት በተለይም በቱሪዝም ዘርፍ የተመዘገበውን ስኬት በዝርዝር አስቀምጠዋል።
በተለይም የገበታ ፕሮጀክቶች ግንባታ፣ የከተሞች ኮሪደር ልማትና የቆዩ ቅርሶች እድሳት ለቱሪዝም ዘርፉ እድገትና ማንሰራራት ትልቅ አቅም እንደሆኑ አንስተዋል።
በዚሁ ጉዳይ ላይ ኢዜአ ካነጋገራቸው የወላይታ ሶዶ ዩኒቨርሲቲ ምሁራን መካከል በዩኒቨርሲቲው የጋዜጠኝነትና የተግባቦት ትምህርት መምህርና ተመራማሪ ተሻለ ተገኔ (ዶ/ር)፤ በኢትዮጵያ በቱሪዝም ዘርፍ ላይ ኢንቨስት ማድረግ የዘርፉን ተወዳዳሪነትና ተመራጭነቷን ያሳድጋል ብለዋል።
ለዚህም መንግስት ተግባራዊ ባደረጋቸው ገበታ ለሸገር፣ ገበታ ለሃገርና ገበታ ለትውልድን ጨምሮ በወንዝ ዳርቻ ልማቶች ያከናወናቸው ተግባራት የዘርፉን ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ፋይዳ እንደሚያጎሉ አንስተዋል፡፡
የልማት ሥራዎቹ የሀገርን ገጽታ ከመገንባት ባለፈ የሥራ ዕድልን ለማስፋት እና የውጭና የሀገር ውስጥ ጎብኚዎችን ቁጥር በመጨመር በኩል የራሱን አስተዋጽኦ ማበርከቱንም ጠቁመዋል።
የለውጡ መንግስት ዘርፉን በፖሊሲ በመምራት የቱሪስት መዳረሻ ስፍራዎች ልማት፣ የአገልግሎት ሰጪ ተቋማትን ማጠናከር እንዲሁም የሰው ሀይል ማፍራት ላይ ትኩረት ማድረጉን ጠቁመዋል።
ይህም የቱሪዝም ዘርፉን እያነቃቃው መሆኑን ገልጸው፣ የዘርፉን ጠቀሜታ ይበልጥ ለማሳደግ ምሁራን በጥናትና ምርምር የመደገፍ ሃላፊነታችንን ማጠናከር ይጠበቅብናል ብለዋል፡፡
በወላይታ ሶዶ ዩኒቨርሲቲ የሥነ ዜጋና ሥነ ምግባር ትምህርት ክፍል መምህርና ተመራማሪ ጣሰው ታደሰ በበኩላቸው እንዳሉት፣ ከለውጡ በፊት በሀገር አቀፍ ደረጃ ጥቂት ታሪካዊ መዳረሻዎች ብቻ ቢኖሩም በበቂ ሁኔታ ሳይለሙ ቆይተዋል።
ይህንን ለመቀየርና ቱሪዝም በሀገር ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴ ላይ ያለውን አበርክቶ ለማሳደግ የለውጡ መንግስት ዘርፉን በፖሊሲ ማሻሻያ ማገዙና መምራቱ የላቁ ውጤቶች እንዲመዘገቡ አድርጓል ብለዋል።
በእዚህም በርካታ የሀገሪቱ ከተሞች የኮንፍረንስ ቱሪዝም ማዕከል እየሆኑ መምጣታቸውን ጠቁመዋል።
የቱሪዝም ዘርፉን ከቴክኖሎጂ ጋር በማስተሳሰር መዳረሻዎች ይበልጥ እንዲተዋወቁ የተጀመሩ ሥራዎች መጠናከር እንዳለባቸውም አክለዋል፡፡