የብዝሃ ዘርፍ ሪፎርሙ የቱሪዝሙን የኢኮኖሚ አበርክቶ አሳድጓል -ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) - ኢዜአ አማርኛ
የብዝሃ ዘርፍ ሪፎርሙ የቱሪዝሙን የኢኮኖሚ አበርክቶ አሳድጓል -ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር)
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 23/2018 (ኢዜአ)፦ የብዝሃ ዘርፍ ሪፎርሙ ለቱሪዝም መስክ የኢኮኖሚ አበርክቶ ማደግ ትልቅ ሚና መጫወቱን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከኤንቢሲ ኢትዮጵያ ጋር ቱሪዝም አዲሱ የኢኮኖሚ ሞተር በሚል ርዕስ ቆይታ አድርገዋል።
መንግስታቸው የጀመረው የብዙሃ-ዘርፍ (Multi-sectoral) የኢኮኖሚ ሪፎርም በአሁኑ ወቅት በአስደናቂ ሁኔታ ውጤት እያስመዘገበ እንደሚገኝም ገልጸዋል።
በግብርናው ዘርፍ በስንዴ፣ በቡና፣ በሩዝ እንዲሁም በፍራፍሬ ልማት የተገኙ ውጤቶች ለሀገር ውስጥ ምርታማነት ትልቅ አስተዋጽኦ እያበረከቱ መሆኑን ጠቁመዋል።
ከዚህም በተጨማሪ እንደ ሌማት ትሩፋት ያሉ ኢኒሼቲቮች፣ የቴክኖሎጂ ሪፎርሞች፣ የመሶብ ፕሮጀክት እና የአምስት ሚሊየን ኮደሮች የስልጠና መርሃ-ግብር ለጠቅላላ የሀገር ውስጥ ምርት (GDP) እድገት የበኩላቸውን ጉልህ ድርሻ እየተወጡ መሆኑን አስገንዝበዋል።
በኢንዱስትሪ እና በማዕድን ዘርፎች የተመዘገቡት ስኬቶችም የኢኮኖሚ ማሻሻያው አካል መሆናቸውን የጠቀሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ሀገሪቱ ከእነዚህ ዘርፎች በርካታ ቢሊየን ዶላሮችን እያገኘች መሆኑን አመልክተዋል።
የተለያዩ የኢኮኖሚ ዘርፎች በየበኩላቸው እያበረከቱት ባለው ሁለንተናዊ ድርሻ ምክንያት የሀገሪቱ ኢኮኖሚ በተከታታይ እያደገ መሆኑን ገልጸው፤ በተያዘው በጀት ዓመት የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ የ 10 ነጥብ 2 በመቶ እድገት ያስመዘግባል ተብሎ እንደሚጠበቅ አስታውቀዋል።
የቱሪዝም ዘርፍን በተመለከተ በዘንድሮው ዓመት ከ1 ነጥብ 4 ሚሊየን በላይ የውጭ ሀገር ጎብኚዎች ኢትዮጵያን የጎበኙ ሲሆን፤ ይህም ቁጥር ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር ከ100 ሺህ በላይ፣ ከካቻምናው አንጻር ደግሞ የ300 ሺህ የጎብኚዎች ጭማሪ ማሳየቱን አብራርተዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ አክለውም የውጭ ቱሪስት ፍሰቱና የተገኘው ገቢ እያደገ ቢሆንም፤ ገና የሚፈለገው ደረጃ ላይ ባይደርስም የታየው ለውጥ ግን እጅግ ተስፋ ሰጪና በግልጽ የሚታይ መሆኑን ገልጸዋል።
ኢትዮጵያ የኮንፈረንስ ቱሪዝም ማዕከል በመሆኗ በበጀት ዓመቱ 204 ዓለም አቀፍ ኮንፈረንሶችን እና ታላላቅ ሁነቶችን ማስተናገዷን ገልጸው፤ ይህም ሀገሪቱ በዓለም አቀፍ መድረክ ያላትን ተሰሚነት ከማሳደጉም በላይ የኮንፈረንስ ቱሪዝም ስበት ማዕከል እየሆነች መምጣቷን ማረጋገጫ ነው ብለዋል።
በሰው ኃይል ልማት፣ በቱሪስቶች ፍሰት፣ በገቢ አሰባሰብ እና በአዋጪነት ረገድ የቱሪዝም ዘርፍ ለመንግስት የሪፎርም ስራዎች ፈጣንና አዎንታዊ ምላሽ እየሰጠ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትሩ አመልክተዋል።
በተለያዩ ጊዜያት ያጋጠሙ ፈተናዎች ቢኖሩም፤ ቱሪዝም ለብሄራዊ ኢኮኖሚው ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ እንደሚገኝና ዘርፉን እንደ አንዱ የኢኮኖሚ ምሰሶ አድርጎ መምረጥና መዋዕለ ንዋይ ማፍሰሱ ፍጹም ትክክለኛ እርምጃ እንደነበር በተከናወኑት ስኬታማ ስራዎች ማረጋገጥ ተችሏል ብለዋል።