ኢትዮጵያ እና ጣሊያን የ70 ሚሊዮን ዩሮ የብድር ስምምነት ተፈራረሙ - ኢዜአ አማርኛ
ኢትዮጵያ እና ጣሊያን የ70 ሚሊዮን ዩሮ የብድር ስምምነት ተፈራረሙ
አዲስ አበባ፤ሰኔ 22/2018(ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ እና ጣሊያን የ70 ሚሊዮን ዩሮ የብድር ስምምነት ተፈራርመዋል፡፡
ስምምነቱ በረጅም ጊዜ የሚከፈል የብድር ስምምነት ሲሆን ለሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ እና የልማት ሥራዎች ማስፈጸሚያ የሚውል መሆኑን የገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሽዴ ገልጸዋል።
የብድር ስምምነቱን የገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሽዴ እና በኢትዮጵያ የጣሊያን አምባሳደር ሴም ፋብሪዚ ተፈራርመውታል።
የገንዘብ ሚኒስትሩ አቶ አሕመድ ሽዴ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ ይህ የብድር ስምምነት በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን ጠንካራ አጋርነት የሚያሳይና የረጅም ጊዜ ታሪካዊ ግንኙነታቸውን ይበልጥ የሚያጠናክር ነው።
ስምምነቱ ቀደም ሲል በሁለቱ ሀገራት መካከል የተደረሱት የትብብር ማዕቀፎች አካል መሆኑንም ጠቁመዋል።
የገንዘብ ድጋፉ ኢትዮጵያ የጀመረቻቸውን ሀገራዊ የኢኮኖሚ ማሻሻያ እርምጃዎችና የልማት ግቦችን ለማሳካት አስተዋፅዖ እንደሚኖረው አስረድተዋል።
ኢትዮጵያ የተሟላ የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርም ተግባራዊ በማድረግ ሁለተኛውን ምዕራፍ በስኬት ማጠናቀቋን ገልጸዋል።
ይህንኑ ተከትሎ የዓለም ባንክ ለሶስተኛው ምዕራፍ የሪፎርም ትግበራ የሚውል የበጀት ድጋፍ ማፅደቁንም አስታውሰዋል።
የጣሊያን መንግሥት ለኢትዮጵያ የልማት ጥረቶችና የኢኮኖሚ ማሻሻያ ለሚያደርገው የገንዘብ ድጋፍና ቀጣይነት ላለው አጋርነት ምስጋና አቅርበዋል።
አምባሳደር ሴም ፋብሪዚ በበኩላቸው፣ የኢትዮጵያ የ10 ዓመት መሪ የልማት ዕቅድ እና የሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ ሀገሪቱን በትክክለኛ የዕድገት አቅጣጫ እየመራት መሆኑን ገልጸዋል።
መንግስታቸውም ይህንን ሂደት በቁርጠኝነት እንደሚደግፍ አረጋግጠዋል።
የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያውን በተግባር ለማገዝ የሚያስችል የ70 ሚሊዮን ዩሮ የብድር ስምምነት ከዓለም ባንክ መርሆዎች ጋር በተጣጣመ መልኩ መፈጸሙን አስታውቀዋል።