የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ የሴቶችን ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት በማረጋገጥ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ ነው - ኢዜአ አማርኛ
የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ የሴቶችን ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት በማረጋገጥ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ ነው
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 21/2018 (ኢዜአ):-የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ የሴቶችን ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት በማረጋገጥ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን የሴቶችና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ገለጸ።
በኢትዮጵያ በ2018 በጀት ዓመት እስከ ሰኔ 30 ቀን ድረስ የፋይዳ መታወቂያ ተጠቃሚዎች ቁጥር ወደ 90 ሚሊየን ለማድረስ ግብ መቀመጡ ይታወቃል።
የብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም ከሴቶችና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ጋር በመተባበር በታህሳስ ወር ”ፋይዳ ለሴቶች” ሀገር አቀፍ የንቅናቄ ማስጀመሪያ መርሃ ግብርን አስጀምሯል።
ሚኒስትር ዴኤታ ሂክማ ከይረዲን ለኢዜአ እንዳሉት፤ የሴቶችን የዲጂታል አገልግሎቶች ተጠቃሚነት ለማላቅ የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ባለቤትነትና ተደራሽነት በስፋት እየተሰራበት ይገኛል።
ከብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራምና ባለድርሻ አካላት ጋር በመተባበርም በሀገር አቀፍ ደረጃ ሴቶች የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ባለቤት እንዲሆኑ እየተደረገ እንደሚገኝ ገልጸዋል።
በእስካሁኑ ሂደት 26 ሚሊየን ሴቶችን የብሔራዊ ዲጂታል መታወቂያ (ፋይዳ) ባለቤት በማድረግ የዲጂታል አገልግሎት ተጠቃሚ እንዲሆኑ እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል።
በዚህም የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ተደራሽነትም የሴቶችን ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት በማረጋገጥ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ እንደሚገኝ ገልጸዋል።
የኦሮሚያ ክልል የሴቶችና ሕፃናት ምክትል ቢሮ ኃላፊ ሰሚራ ፋሪስ፤ በከተማና ገጠር የሚኖሩ የክልሉ ሴቶች የዲጂታል መታወቂያ ባለቤት እንዲሆኑ እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል።
የሴቶች የዲጂታል መታወቂያ ባለቤትነትም ሁለንተናዊ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ የልማት ተጠቃሚነትን እያረጋገጠ መሆኑን ተናግረዋል።
በአማራ ክልል ሴቶች፣ ወጣቶችና ማኅበራዊ ጉዳይ ቢሮ ምክትል ኃላፊ ዝና ጌታቸው በበኩላቸው፤ የሴቶችን የዲጂታል መታወቂያ ባለቤትነት ለማረጋገጥ በበጎ ፈቃድ አገልግሎት ጭምር እየተሰራበት ነው ብለዋል።
በዚህም ከባድርሻ ተቋማት ጋር በመተባበር በተከናወነ ሥራ በ2018 ዓ.ም እስካሁን ድረስ ከ5 ሚሊየን በላይ የክልሉ ሴቶች የዲጂታል መታወቂያ ባለቤት ማድረግ መቻሉን አስታውቀዋል።
በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የሴቶችና ሕፃናት ጉዳዮች ቢሮ ምክትል ኃላፊና የሴቶች ዘርፍ ኃላፊ ነጅሚያ ራህመቶ በበኩላቸው፤ የተለያዩ አደረጃጀቶችን በመጠቀም ሴቶች የዲጂታል መታወቂያ ባለቤት እንዲሆኑ እየተደረገ ነው ብለዋል።
በዚህም የአደረጃጀቶችን ንቅናቄ በመጠቀም ከ1 ነጥብ 5 ሚሊየን በላይ ሴቶችን የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ባለቤት ማድረግ እንደተቻለ አስረድተዋል።
በጋምቤላ ክልል የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ ኃላፊ አረየት ዑጁሉ በበኩላቸው፤ በክልሉ የግንዛቤ ማስጨበጫ ንቅናቄ በማካሄድ ሴቶች የዲጂታል መታወቂያ ባለቤት እንዲሆኑ እየተደረገ ነው ብለዋል።
ይህም በተለያዩ አገልግሎቶች ላይ የሴቶችን ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት በማረጋገጥ የልማት አካል እንዲሆኑ እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል።