በክልሉ ህዝቡ ሲያቀርባቸው የነበሩ የልማት ጥያቄዎችን የፈቱ ፕሮጀክቶች በጥራት ተገንብተው ለአገልግሎት እየበቁ ነው - ኢዜአ አማርኛ
በክልሉ ህዝቡ ሲያቀርባቸው የነበሩ የልማት ጥያቄዎችን የፈቱ ፕሮጀክቶች በጥራት ተገንብተው ለአገልግሎት እየበቁ ነው
ሆለታ ሰኔ 20/2018 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ህዝቡ ለረጅም ጊዜ ሲያቀርባቸው የነበሩ የልማት ጥያቄዎችን የፈቱ ፕሮጀክቶች በፍጥነትና በጥራት ተገንብተው ለአገልግሎት እየበቁ መሆኑን የክልሉ ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ አወሉ አብዲ አስታወቁ።
በሆለታ ከተማ ዛሬ ከ700 ሚሊየን 413 ሺህ ብር በላይ በሆነ ወጪ የተገነቡ ልዩ ልዩ ፕሮጀክቶች ተመርቀው ለአገልግሎት ክፍት ሆነዋል።
በከተማው ለአገልግሎት ከበቁ ፕሮጀክቶች መካከል የከተማ አስተዳደሩ ባለ 5 ወለል ህንፃ፣ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት፣ የይግባኝ ሰሚ ባህላዊ ፍርድ ቤት፣ የዶሮ እርባታ ክላስተር ማዕከል፣ የኮሪደር ልማት እና የጎጆ ኢንዱስትሪዎች መሆናቸው ተገልጿል።
በምረቃ ሥነ-ሥርዓቱ ላይ የኦሮሚያ ክልል ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ አወሉ አብዲ እንደተናገሩት በክልሉ ከለውጡ ወዲህ የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡና ለረጅም ጊዜ ሲያቀርባቸው የነበሩ የልማት ጥያቄዎችን የፈቱ ፕሮጀክቶች በፍጥነትና በጥራት ተገንብተው ለአገልግሎት እየበቁ ነው።
በተለይም ከተሞችን ለኑሮ ምቹ እንዲሁም የምርትና ምርታማነት ማዕከል ማድረግ፣ ቀልጣፋ፣ ፍትሐዊና ጥራት ያለው የመንግሥት አገልግሎት መስጫ ስፍራ እየሆኑ ነው ብለዋል።
የሆለታ ከተማ በአዲስ አበባ በቅርብ ርቀት የምትገኝና ረጅም ዕድሜ ያላት ብትሆንም፣ ቀደም ሲል በሚፈለገው ደረጃ ያልለማች ከተማ ነበረች ብለዋል።
ከለውጡ ወዲህ ግን በከተማዋ እየተከናወነ ባለው ሥራ ከተማዋ ለኑሮ ምቹ፣ የምርታማነት ማዕከል እየሆነች መምጣቷን ገልጸዋል።
አዲሱ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ማዕከል ዜጎች የዲጂታል ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም የመንግሥት ልዩ ልዩ አገልግሎቶችን በአንድ ቦታ እንዲያገኙ የሚያስችል ሲሆን፣ በማዕከሉ የተመደቡ ባለሙያዎችም የተጣለባቸውን አደራ በታማኝነት እንዲወጡ አሳስበዋል።
የሆለታ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ እሸቱ በቀለ በበኩላቸው፤ ዛሬ የተመረቁት ፕሮጀክቶች የከተማዋን የልማት ዕቅድ ከማሳካት ባለፉት ዓመታት ከተከናወኑት ሰፊ ሥራዎች መካከል ትልቅ ውጤት ናቸው ብለዋል።
በተለይም በ541 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ የተገነባው ባለ አምስት ወለል የከተማ አስተዳደር ሕንፃ የቢሮዎችን እጥረት በመቅረፍና ከአገልግሎት አሰጣጥ ጋር ተያይዞ የሚነሱ ቅሬታዎችን ለመፍታት ያስችላል ብለዋል።
ይህ መዋቅር የአገልግሎት ፈላጊዎችን እንግልት በማስቀረትና አላስፈላጊ ወጪን እንደሚያስቀር አብራርተዋል።
ከንቲባው አክለውም እነዚህ ፕሮጀክቶች የሥራ ዕድልን ለማስፋፋትና የማህበረሰቡን ኑሮ ለማሻሻል ጠንካራ መሠረት መሆናቸውን ጠቅሰው፤ ማህበረሰቡ በከፍተኛ የመንግሥትና የሕዝብ ሀብት የተገነቡትን ንብረቶች በአግባቡ ጠብቆ በመጠቀም ለልማቱ ቀጣይነት የበኩሉን ሚና እንዲወጣ ጥሪ አቅርበዋል።