በኦሮሚያ ክልል እየተገነቡ ያሉ የመሰረተ ልማት ተቋማት የህዝቡን የልማት ጥያቄዎች በተጨባጭ እየመለሱ ነው - ኢዜአ አማርኛ
በኦሮሚያ ክልል እየተገነቡ ያሉ የመሰረተ ልማት ተቋማት የህዝቡን የልማት ጥያቄዎች በተጨባጭ እየመለሱ ነው
አዳማ፣ ሰኔ 20/2018 (ኢዜአ)፡– በኦሮሚያ ክልል እየተገነቡ ያሉ የልማት ፕሮጀክቶች የህዝቡን የመልማት ጥያቄዎች በተጨባጭ እየመለሱ መሆናቸውን በብልፅግና ፓርቲ የክልሉ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ከፍያለው ተፈራ ገለፁ።
የክልሉ መንግስት ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች በተገኙበት ዘርፈ ብዙ አገልግሎት የሚሰጠው የ'አዳማ ሲቲ አሬና' ወይም የህዝብ አደባባይ ዛሬ በይፋ ተመርቆ ለአገልግሎት ክፍት ሆኗል።
ዛሬ ተመርቆ ለአገልግሎት የበቃው ይኸው ሁለገብ ማዕከል የህዝባዊ ኩነቶችና ዝግጅቶች ማስተናገጃ ስፍራ፣ ዘመናዊ የዳታ ማዕከል፣ ቤተ-መጻሕፍት እና የካፌቴሪያ አገልግሎቶች፣ የገበያ ማዕከልና የስፖርት መዘውተሪያ ስፍራዎች፣ ሰፊ የመኪና ማቆሚያ ያለው መሆኑ ተመልክቷል።
በምረቃ ሥነ-ሥርዓቱ ላይ በብልፅግና ፓርቲ የኦሮሚያ ክልል ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ከፍያለው ተፈራ፣ ባለፉት አምስት ዓመታት በክልሉ በርካታ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች ተጠናቀው ለህዝብ አገልግሎት በቅተዋል።
በመጠናቀቅ ላይ ባለው በዚህ በጀት ዓመት ብቻ ከ28 ሺህ በላይ ፕሮጀክቶች በሁለት ምዕራፎች ተመርቀው ለአገልግሎት ክፍት መደረጋቸውን ጠቁመዋል።
ዛሬ የተመረቀው የአዳማ ከተማ የህዝብ አደባባይ የ'ስማርት አዳማ' ግቦችን ለማሳካት ከማገዙ ባለፈ፣ በአገልግሎት አሰጣጥና በመልካም አስተዳደር ረገድ የሚታዩ ችግሮችን በዘላቂነት ለመቅረፍ ይረዳል ብለዋል።
በክልሉ ባለፉት ዓመታት ለአገልግሎት የበቁ የመሰረተ ልማት ተቋማት በተጨባጭ ህዝቡን ተጠቃሚ ማድረግ መቻላቸውን ገልጸው፣ በቀጣይም ስራ አጥነትና የአገልግሎት አሰጣጥ ችግሮችን ለመቀነስ የተጀመሩ ስራዎች ይጠናከራሉ ብለዋል።
የክልሉ ነዋሪም በየአካባቢው ለተገነቡ ፕሮጀክቶች ተገቢው ክትትልና እንክብካቤ ሊያደርግላቸው እንደሚገባ አስገንዝበዋል።
የአዳማ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ኃይሉ ጀልዴ በበኩላቸው፣ የልማት ፕሮጀክቶቹ ለህዝብ የገባነውን ቃል በተግባር ያረጋገጥንባቸውና የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት እውን ያደረጉ ናቸው ብለዋል።
ባለፉት ዓመታት በከተማዋ የተከናወኑ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ፕሮጀክቶች በተያዘላቸው ጊዜ ተጠናቀው ለአገልግሎት መብቃታቸውንም ገልጸዋል።
ከተማዋን የኢንዱስትሪ ማዕከል ለማድረግና ስራ አጥነትን ለመቀነስ በተከናወኑ ተግባራት ተስፋ ሰጪ ውጤቶች መመዝገባቸውን ገልጸዋል።
በተለይም የኮሪደር ልማት ስራዎች መሳካታቸውን፣ የመንግስት አገልግሎትና የሀብት አስተዳደር ሥርዓት መዘመኑን፣ የመሬት ሀብት አስተዳደር ከውስብስብ ችግሮች ወጥቶ ለልማት አጋዥ መሆኑን ጠቅሰዋል።
ይህ የአሰራር ማዘመን ሂደት የከተማዋን ገቢ ከማሳደጉም በላይ፣ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ የልማት ስራዎችን በራስ አቅም ለመሸፈን ትልቅ አቅም መፍጠሩን አቶ ኃይሉ አብራርተዋል።