ቀጥታ፡

የድጋፍና የብድር ስምምነቶቹ ኢትዮጵያ የምታከናውናቸው የልማት ተግባራት ተጨባጭ ውጤቶችን እያመጡ መሆኑን አመላካች ናቸው

አዲስ አበባ፤ሰኔ 19/2018 (ኢዜአ)፦የድጋፍና የብድር ስምምነቶቹ ኢትዮጵያ የምታከናውናቸው የልማት ተግባራት ተጨባጭ ውጤቶችን እያመጡ እንደሚገኙ አመላካች መሆናቸውን የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ገለጹ።

የገንዘብ ሚኒስትሩ አሕመድ ሽዴ በበኩላቸው ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያው ዘመናዊ የኢኮኖሚ አስተዳደር ሥርዓትን በመገንባት ረገድ ገንቢ ሚና ማበርከቱን ተናግረዋል።

6ኛው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 1ኛ ልዩ ስብሰባ በዛሬው ዕለት ተካሂዷል።

ምክር ቤቱ ባካሄደው ልዩ ስብሰባ ከዓለም አቀፍ የልማት ማህበር ጋር የተፈረሙ ሦስት የፋይናንስ ድጋፍና ብድር ስምምነት አዋጆችን አጽድቋል፡፡

የገንዘብ ሚኒስትሩ አሕመድ ሽዴ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ ባለፉት ዓመታት የተተገበረው የተሟላ ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ የፋይናንስ ዘርፉን በማረጋጋት ረገድ አወንታዊ ሚና አበርክቷል፡፡

በተለይ ደግሞ የገቢ አሰባሰብንና የውጭ ምንዛሬ መጠንን በከፍተኛ መጠን ማሳደጉን ተናግረዋል፡፡

ሪፎርሙ ዘመናዊ የኢኮኖሚ አስተዳደር ሥርዓትን በመገንባት ረገድ ገንቢ ሚና መጫወቱንም ነው የገለጹት፡፡

ከዓለም አቀፍ የልማት ማህበር ጋር የተፈረሙ የድጋፍና ብድር ስምምነቶች በፋይናንስ፣ በንግድ፣ በአየር ንብረት ለውጥ፣ በኢነርጂ፣ በመሠረተ ልማት፣ በግብርና እና በሌሎች ዘርፎች እየተከናወኑ ያሉ ተግባራትን ለመደገፍ የሚውሉ ናቸው ብለዋል፡፡

የወጣቶችን፣ ሴቶችን፣ የአርሶና አርብቶ አደሮችን ሕይወት ለማሻሻል በሚደረገው ርብርብ ትልቅ የፋይናንስ አቅም እንደሚፈጥሩም ጠቁመዋል።

የአየር ንብረት ለውጥን በመከላከል አረንጓዴ ኢኮኖሚን ለመገንባትና የመስኖ ልማቶችን ለማዘመን እንደሚያግዙም እንዲሁ።

የምክር ቤት አባላት በበኩላቸው፤ የድጋፍና የብድር ስምምነቶቹ ኢትዮጵያ የምታከናውናቸው የልማት ተግባራት ምን ያህል ለውጥ እያመጡና የሕብረተሰቡን ሕይወት በተጨባጭ እየቀየሩ በመሆኑ የተገኙ ናቸው ብለዋል።

ለተጀመሩ የልማት ፕሮጀክቶች መሳካትም ትልቅ የፋይናንስ አቅም እንደሚሆኑ ተናግረዋል፡፡

ምክር ቤቱ በልዩ ስብሰባው ከጤና፣ ማኅበራዊ ልማት፣ ባህልና ስፖርት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የቀረበለትን ሪፖርት መርምሮ የምግብ ሥርዓትና ሥርዓተ ምግብ አዋጅን አጽድቋል፡፡

በተመሳሳይ ከግብርና ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የቀረበለትን የግብርና ቢዝነስ ካምፓኒ ረቂቅ አዋጅን መርምሮ አጽድቋል፡፡
#Ethiopian_News_Agency
#ኢዜአ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም