ቀጥታ፡

ፋይዳ የዲጂታል አገልግሎትን በማስፋት ፈጠራን ማዕከል ያደረጉ ዘመናዊ ተቋማትን መገንባት አስችሏል

አዲስ አበባ፤ ሰኔ 19/2018 (ኢዜአ)፦ የብሔራዊ ዲጂታል መታወቂያ (ፋይዳ) የዲጂታል አገልግሎትን በማስፋት ፈጠራን ማዕከል ያደረጉ ዘመናዊ ተቋማትን መፍጠር እያስቻለ መሆኑን የብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም ገለጸ፡፡

በኢትዮጵያ የነዋሪዎችን የመታወቅ መብት ለማረጋገጥ፣ በአገልግሎት ሰጭና ተቀባዮች መካከል መተማመንን ለማዳበር፣ በሀገር አቀፍ ደረጃ ግልጽነት፣ ተጠያቂነትና የተሳለጠ አሰራር ለማንበር የዲጂታል መታወቂያ ገቢራዊ ተደርጓል፡፡

በዚህም የኢትዮጵያ ዲጂታል መታወቂያ በአዋጅ ቁጥር 1284/2015 ተቋቁሞ ወደ ስራ ገብቶ እስካሁን ከ46 ሚሊየን በላይ ዜጎች  ተመዝግበው የዲጂታል መታወቂያ ባለቤት ሆነዋል፡፡

የብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም የግንኙነትና የባለድርሻ አካላት ዳይሬክተር ሳሚናስ ሰይፉ ለኢዜአ እንዳሉት፤ በመላ ሀገሪቱ በ12 የምዝገባ ማሽኖች የብሔራዊ ዲጂታል መታወቂያ ምዝገባ እየተከናወነ ነው፡፡

ምዝገባው በኢትዮ ቴሌኮም፣ ኢትዮ-ፖስታ፣ በባንኮችና ለሌሎች አጋር ተቋማት የሚከናወን ሲሆን ተመዝጋቢዎች ፈጣን አገልግሎት የሚያገኙበት አሰራር ተዘርግቷል ብለዋል፡፡

በፕሮግራሙ በቀን ከሁለት ሚሊየን በላይ መረጃዎች እየተረጋገጡ ሲሆን እስካሁን የተረጋገጠላቸው ደንበኞች ቁጥር 104 ሚሊየን መድረሱን ገልጸዋል፡፡

የብሔራዊ ዲጂታል መታወቂያ አገልግሎት የራስን ማንነት የመለያና ወደ ኢኮኖሚ የመግቢያ መንገድ መሆኑን ገልጸው፤ ማህበራዊ አገልግሎትን በቀላሉ ማግኘት ያስችላል ብለዋል፡፡

ፋይዳ ሚናው ማጭበርበርን ማስቀረት ብቻ አይደለም ያሉት ዳይሬክተሩ፤ ፈጠራና ዘመናዊነትን የተላበሱ ተቋማትን መፍጠር እንደሚያስችል ገልጸዋል፡፡

በተቋማት መካከል መተማመን እንዲፈጠር እያደረገ መሆኑን በማነሳት፤ መሶብ የአንድ ማዕከል ዲጂታል አገልግሎት በርካታ አገልግሎቶችን በአንድ ጊዜና ቦታ መስጠቱን ለአብነት ጠቅሰዋል፡፡

ከዚህም ባለፈ ሀገር ለዜጎቿ ግልጽ ዕቅድ በማውጣት ተገቢውን በጀት ለመመደብ ተጨባጭ ማስረጃ ሆኖ ያገለግላልም ብለዋል፡፡

ከፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ሥርዓት ጋር የተሳሰሩ ተቋማት 150 መድረሳቸውን በማንሳት፤ የምዝገባ ሽፋኑን ወደ ሁሉም የገጠሪቱ አካባቢ ለማስፋት ተጨማሪ ግዙፍ ወኪሎችን ወደ ሥራ እንደሚገቡም ጠቁመዋል፡፡

 

 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም