ቀጥታ፡

ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ የመንገድ ደህንነት ግቦችን ከአገሪቱ ነባራዊ ሁኔታ ጋር አጣጥማ እየተገበረች ነው

አዲስ አበባ፤ ሰኔ 19/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ የመንገድ ደህንነት ግቦችን ከአገሪቱ ነባራዊ ሁኔታ ጋር አጣጥማ እየተገበረች መሆኑ ተገለጸ፡፡ 

የመንገድ ደህንነት መድን ፈንድ አገልግሎት በመንገድ ትራፊክ አደጋ የሚደርሰውን ሞት ፣ የአካል ጉዳትና የንብረት ውድመት ለመቀነስ በዘርፉ የተቀመጡ ሀገራዊና ዓለም አቀፋዊ ግቦችን ለማሳካት የግማሽ ዘመን ስትራቴጂ አፈፃፀም ላይ ሀገር አቀፍ ጉባኤ እያካሄደ ይገኛል።


 

የኢትዮጵያ የመንገድ ደህንነትና መድን ፈንድ አገልግሎት ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ጀማል አባሶ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ በኢትዮጵያ ደህንነቱ የተጠበቀ የትራፊክ ፍሰት ለመፍጠር የተጀመሩ የስትራቴጂክ ስራዎች ተጨባጭ ፍሬ ማፍራት ጀምረዋል፡፡ 

አገልግሎቱ የትራፊክ አደጋ ስጋትን ለመቀነስ በቅንጅት ያከናወናቸው ተግባራት ተስፋ ሰጪ ውጤት እያስገኙ መሆናቸውንም ተናግረዋል፡፡

በተከናወኑት ስልታዊ የቅድመ-መከላከል ስራዎች ምክንያት የአደጋው ቁጥር ጉልህ መሻሻል እያሳየ መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡ 

የወርልድ ሪሶርስ ኢንስቲትዩት (WRI) ከፍተኛ ባለሙያ ኢንጂነር ሰመረ ጅላሉ በበኩላቸው፤ ከ2021 እስከ 2030 የተቀመጡትን ዓለም አቀፍ የመንገድ ደህንነት ግቦች ለማሳካት በርካታ ስኬታማ ተግባራት ማከናወኗን ተናግረዋል፡፡ 

በዚህም ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ የመንገድ ደህንነት ግቦችን ከአገሪቱ ነባራዊ ሁኔታ ጋር አጣጥማ እየተገበረች መሆኗን ገልጸዋል፡፡   

በሕብረተሰቡ ዘንድ በትራፊክ አደጋ ተጋላጭነት ዙሪያ ሰፊ የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራዎች ሲከናወኑ የቆዩ ሲሆን፣ በቀጣይም ተግባራቱ ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ በመድረኩ ተጠቅሷል፡፡  

በዚሁ ሀገር አቀፍ ጉባኤ ላይ የኢትዮጵያ የመንገድ ደህንነትና መድን ፈንድ አገልግሎት በዲጂታል የታገዘ የትራፊክ አደጋ መረጃ አስተዳደር ሥርዓት ለኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን አስረክቧል፡፡   

 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም