ኢትዮጵያ የሳይበር ደህንነት ሥጋትን መከላከልና ሊከሰቱ ለሚችሉ አደጋዎች ፈጣን ምላሽ የሚሰጥ ትልቅ ተቋም ገንብታለች - ኢጋድ - ኢዜአ አማርኛ
ኢትዮጵያ የሳይበር ደህንነት ሥጋትን መከላከልና ሊከሰቱ ለሚችሉ አደጋዎች ፈጣን ምላሽ የሚሰጥ ትልቅ ተቋም ገንብታለች - ኢጋድ
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 19/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የሳይበር ደህንነት ሥጋትን መከላከልና ሊከሰቱ ለሚችሉ አደጋዎች ፈጣን ምላሽ መስጠት የሚችል ትልቅ ተቋም መገንባቷን የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት ባለስልጣን /ኢጋድ/ ገለጸ፡፡
የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት ባለስልጣን (ኢጋድ) ከኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ጋር በመተባበር ያዘጋጀው የኢጋድ ቀጣናዊ የሳይበር የተግባር ልምምድ ስልጠና በአዲስ አበባ እየተካሄደ ነው፡፡
በመርሃ ግብሩ ላይ የኢትዮጵያን ጨምሮ ዩጋንዳ፣ ኬንያ፣ ሱዳን፣ ደቡብ ሱዳን፣ ሶማሊያ እና የጅቡቲ ተወካዮች ተገኝተዋል፡፡
በኢትዮጵያ የኢጋድ ተጠሪ አበባው ቢሆነኝ እንዳሉት፤ የሳይበር ደህንነት ስጋት በአንድ ሀገር ብቻ የተገደበ ሳይሆን ድንበር ተሻጋሪ ዓለም አቀፍ ሥጋት ነው፡፡
ዓለም በደረሰበት የዲጂታል አብዮት ዘመን የሳይበር ደህንነት ሥጋት ዓለም አቀፍ የጋራ ሥጋት እየሆነ መምጣቱን ገልጸዋል፡፡
በመሆኑም የኢጋድ አባል ሀገራት በመተባበርና ተቋማዊ አሰራራቸውን በማጠናከር ቁልፍ መሠረተ ልማቶቻቸውን በጋራ መጠበቅ ይገባቸዋል ብለዋል፡፡
የሳይበር ደህንነት አደጋን መከላከል የሚቻለውም በጋራ ነው ያሉት ተጠሪው፤ የኢጋድ አባል ሀገራት ድንበር ተሻጋሪ የሳይበር ደህንነት ስጋትን መከላከልና ፈጣን ምላሽ መስጠት የሚያስችል ትብብር መፍጠር እንዳለባቸው ገልጸዋል፡፡
የኢትዮጵያ ኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ከቀጣናው ሀገራት ሁሉ የተደራጀና ጠንካራ ተቋም መሆኑን ገልጸው፤ ኢጋድ ያዘጋጀው የተግባር ስልጠናም በሀገራት መካከል ልምድ መለዋወጥ ያስችላል ብለዋል፡፡
ኢጋድ አባል ሀገራቱ የሳይበር ደህንነት ሥጋትን ለመከላከልና አደጋ ሲደርስ ፈጣን ምላሽ መስጠት የሚችሉበትን የአቅም ግንባታ ስልጠና አጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልጸዋል፡፡
የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ዋና ዳይሬክተር ትዕግስት ሃሚድ፤ የሀገሪቱን ቁልፍ የመሠረተ ልማቶች የመጠበቅ ኃላፊነቱን በብቃት መወጣት የሚያስችል ተቋማዊ አደረጃጀት ተፈጥሯል ብለዋል፡፡
የኢትዮጵያን የሳይበር ደህንነት ስጋት ለመከላከልና አደጋ ሲደርስ ፈጣን ምላሽ ለመስጠት 24 ሰዓት ሙሉ የሚሰራ "Cyber Emergency and Response Team" ተቋቁሞ እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
በቴክኖሎጂ፣ በአሰራር ስርዓት፣ በህግ እና መመሪያ የተደገፈ ትልቅ የሳይበር ደህንነት ቁመና ላይ እንገኛለንም ብለዋል፡፡
የሳይበር ጥቃት ዓለም አቀፍ ስጋት መሆኑን በመረዳት ከዓለም አቀፍ፣ አህጉራዊና ቀጣናዊ የሳይበር ተቋማት ጋር በትብብር መሥራት የሚያስችል ስምምነት መፈራረማቸውን ገልጸዋል፡፡
ኢትዮጵያ ለአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ የንግድ ቀጣና ትግበራ እና ለአጀንዳ 2063 መሳካት ኃላፊነት እንዳለባት ሀገር ግቦችን እውን ለማድረግ ቀጣናዊ ትስስር እንዲፈጠር አበክራ ትሰራለች ብለዋል፡፡
ከለውጡ በፊት በቀጣና ደረጃ ስለ ሳይበር ደህንነት ተወያይተን አናውቅም ነበር ያሉት ዋና ዳይሬክተሯ፤ አሁን ላይ ለጎረቤት ሀገራት ቅድሚያ በሚሰጠው የውጭ ግንኙነት ፖሊሲ ከቀጣናው ሀገራት ጋር በትብብር እየሰሩ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
ኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር የኢትዮጵያን የዲጂታል ድንበር የሚጠብቅ ተቋም መሆኑን ገልጸው፤ ዓለም አቀፉ የቴሌኮሙኒኬሽን ህብረት ባወጣው የሳይበር ደህንነት ቁመና ከነበርንበት 26 ነጥብ ወደ 76 ከፍ ብለናል ብለዋል፡፡
ዓለም አቀፉ የቴሌኮሙኒኬሽን ህብረት አማካሪ ዲጂት ኦክታቭራንቶ በበኩላቸው፤ የሳይበር ደህንነት ሥጋትን ለመከላከል የዲጂታል መሠረተ ልማት ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
ሰው ሰራሽ አስተውሎት የዓለምን የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂና የሳይበር ደህንነት ቁመና መቀየሩን ገልጸው፤ ዘመኑን የዋጀ የሳይበር ደህንነት መሠረተ ልማት መገንባት ይገባል ብለዋል፡፡
በአፍሪካ ብሎም በኢጋድ ቀጣና የሳይበር ደህንነት ሥጋትን በመከላከልና ለአደጋዎች ምላሽ በመስጠት የባህል፣ የቴክኖሎጂና የዕውቀት ልዩነት እንዳለ መታዘባቸውንም ገልጸዋል፡፡
ከዚህ አንጻር ኢትዮጵያ የሳይበር ደህንነት ሥጋትን ለመከላከል ሰፊ መሠረተ ልማት በመገንባት ወሳኝ ሂደት ላይ መሆኗን ተናግረዋል፡፡
በኢትዮጵያ ሁሉም ነገር ወደ ዲጂታል ስርዓት እየተሸጋገረ መሆኑን ገልጸው፤ ይሄ ደግሞ የሳይበር ደህንነት ስጋትን መከላከል ያስችላል ብለዋል፡፡