ከአፍሪካ ትልሞች ጋር የተሳሰረው የኢትዮጵያ ሜጋ ፕሮጀክቶች ስኬት - ኢዜአ አማርኛ
ከአፍሪካ ትልሞች ጋር የተሳሰረው የኢትዮጵያ ሜጋ ፕሮጀክቶች ስኬት
ኢትዮጵያ በታሪክ አጋጣሚዎች በአፍሪካ የነጻነት ትግል ግንባር ቀደም በመሆን፣ የቅኝ ግዛት ቀንበርን በመስበር ለቀሪው አህጉር የተስፋ ብርሃን የፈነጠቀች ሀገር ናት።
ዛሬም፣ኢትዮጵያ ይህንን ታሪካዊ አደራ በመቀጠል፣ በሜጋ ፕሮጀክቶቿ ስኬት የአፍሪካን የኢኮኖሚ ነጻነትና ትስስር በመምራት ላይ ትገኛለች።እንደ ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ፣ የቢሾፍቱ አለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ፣ የጎዴ የዩሪያ ማዳበሪያ ፋብሪካ፣የኦጋዴን ፈሳሽ የተፈጥሮ ጋዝ ፕሮጀክት እንዲሁም በሌሎች ዘርፎችም ጭምር ከሀገር ስኬት ባሻገር የአህጉሪቱን የልማት ህልም እውን የሚያደርጉ ቁልፍ መሰረተ ልማቶች በመከወን ላይናቸው።
የአፍሪካ የኢኮኖሚ ዕድገት ዋነኛው ማነቆ የኃይል አቅርቦት እጥረት መሆኑ አጠያያቂ አይደለም።ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ለኢትዮጵያ የኤሌክትሪክ ፍላጎት ማሟያ ብቻ ሳይሆን፣ለቀጠናው አገራት አስተማማኝ የኃይል ምንጭ በመሆን የአፍሪካን የኢንዱስትሪ ሽግግር የሚያፋጥን የኃይል ማዕከል በመሆን ለቀጣናው የቀረበ ውድ ስጦታ ነው። ይህ ፕሮጀክት አፍሪካ በራሷ ሃብት ተጠቅማ የኃይል ዋስትናዋን ማረጋገጥ እንደምትችል የሚያሳይ በራስ የመተማመን ምልክት ነው።
ኢትዮጵያ በሜጋ ፕሮጀክቶቿ የምትገነባው የሎጂስቲክስ አውታርም፣ ለአፍሪካ የንግድ ትስስር እውን መሆን ወሳኝ ነው።የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ግንባታ ለቀጣዩ የአህጉሪቱ የዕድገት ምዕራፍ የተዘጋጀ ስልታዊ ምላሽ ከመሆኑም በላይ፣ የኢትዮጵያን ብልጽግና ከአፍሪካ ብልጽግና ጋር የሚያቆራኝ ወሳኝ የሜጋ ፕሮጀክት ነው።
አፍሪካ በራሷ ጥረት የዓለም አቀፍ ደረጃ መሰረተ ልማቶችን መገንባት እንደምትችል ኢትዮጵያ በእዚህ ፕሮጀክቷ በኩል መልዕክት እያስተላለፈች ነው።ይህ አውሮፕላን ማረፊያ ኢትዮጵያን በአህጉሪቱ የልማት ግንባር ቀደምትነቷን የሚያጸና፣ እንዲሁም የነገውን የአፍሪካ ህልም ወደ ተግባር የሚቀይር የልህቀት ማማ ነው።
የኢትዮጵያ ሜጋ ፕሮጀክቶች ስኬት ከአፍሪካ የልማት ትልም ጋር የተሳሰረበት ሌላው ቁልፍ ምክንያት አፍሪካ ያለ ውጭ ዕርዳታና ጣልቃ ገብነት፣በራሷ ህዝብ ሃብትና ጥረት ግዙፍ ፕሮጀክቶችን መገንባት እንደምትችል ኢትዮጵያ በተግባር እያሳየች ነው።ይህ ለሌሎች የአፍሪካ አገራት ታላቅ የልማት ተምሳሌት ነው።
የቴክኖሎጂ ሽግግርን፣የባለሙያ አቅም ግንባታን እንዲሁም የፕሮጀክት አመራር ክህሎትን በማጎልበት፣ኢትዮጵያ የአፍሪካን የሰው ሃይል ለለውጥ እያዘጋጀች ስለመሆኑ አያጠራጥርም።
የሜጋ ፕሮጀክቶቹ ተፅዕኖ ከኢትዮጵያ ድንበር አልፎ በምስራቅ አፍሪካ ቀጠና ላይ ያለው ፋይዳ ከፍተኛ ነው።ቀጠናዊ የኃይል አቅርቦት፣የንግድ መስመሮች፣ እንዲሁም የኢንዱስትሪ መዳረሻዎች መፈጠር፣ ለጎረቤት አገራት የኢኮኖሚ እድገት የጋራ ማጠንጠኛ ሆነዋል።
ኢትዮጵያ የምትከተለው የልማት ጎዳና ከድህነት እና ከግጭት ወጥመድ በማውጣት፣ ወደ የጋራ ብልጽግና የሚያመራውን የአፍሪካ ህብረት የ2063 ራዕይ እያሳካ ይገኛል።
ኢትዮጵያ በታሪክ አፍሪካ ነጻነቷን እንድታውጅ ከፊት ሆና እንደመራችው ሁሉ፣ ዛሬም በሜጋ ፕሮጀክቶቿ አማካኝነት አፍሪካ ከድህነት ተላቃ የኢኮኖሚ ነጻነቷን እንድታረጋግጥ መሪ ፊታውራሪ ሆናለች።
እነዚህ ፕሮጀክቶች የኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆኑ፣የአፍሪካ የኩራት ምንጭና የህልውና መሰረቶች ናቸው።ኢትዮጵያ እያከናወነች ያለው የልማት እንቅስቃሴ፣ አፍሪካ በራሷ መንገድ የራሷን የልማት ታሪክ እየጻፈች መሆኗን የሚያረጋግጥ ነው።
በመሆኑም የኢትዮጵያ ሜጋ ፕሮጀክቶች ስኬት፣የነገዋ አፍሪካ በዓለም መድረክ ያላት ተጽዕኖ መገለጫ፣ እንዲሁም የጋራ የወደፊት ብልጽግናዋ ዋስትና ናቸው።