ቀጥታ፡

በምዕራብ ሸዋ ዞን የህዝቡን የልማት ጥያቄዎች የሚመልሱ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች ለአገልግሎት በቁ

አምቦ፤ሰኔ 18/2018 (ኢዜአ):- በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ሸዋ ዞን የህዝቡን የቆዩ የልማት ጥያቄዎች ለመፍታት የተገነቡ የተለያዩ የመሰረተ ልማት አውታሮች በሁለት ዙር ተመርቀው ለአገልግሎት ክፍት መሆናቸውን የዞኑ አስተዳደር አስታወቀ።

በዞኑ ኢሉ ገላን ወረዳ ተገንብተው ለአገልግሎት የበቁት ኮሪደር ልማት፣ የእንስሳት ጤና ኬላ፣ የቅድመ መደበኛ ትምህርት ቤት እና ሌሎች የመሰረተ ልማት ተቋማትም ይገኙበታል።

በምረቃ ሥነ ሥርዓቱ ላይ የተገኙት የምዕራብ ሸዋ ዞን አስተዳዳሪ አቶ ዲዳ ጉደታ እንደገለጹት፤ በዞኑ በሕዝብና በመንግሥት ትብብር የተገነቡ የልማት ፕሮጀክቶች ለአገልግሎት እየበቁ ነው።


 

በበጀት ዓመቱ በመጀመሪያው ዙር 391 የልማት ፕሮጀክቶች ተመርቀው አገልግሎት መጀመራቸውን የገለጹት አስተዳዳሪው፤ የሁለተኛው ዙር ምረቃ በኢሉ ገላን ወረዳ መጀመሩን ጠቁመዋል።

ግንባታቸው ተጠናቆ ምርቃታቸው የተጀመረው የሁለተኛ ዙር ፕሮጀክቶች ቁጥር 128 መሆኑንም ገልጸዋል።

የኢሉ ገላን ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ አሚን ነሻ በበኩላቸው፤ በወረዳው በመንግሥት በጀትና በሕብረተሰቡ ተሳትፎ ከ106 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ የተገነቡ 18 የልማት ፕሮጀክቶች ተጠናቀው ለአገልግሎት ክፍት መሆናቸውን አስታውቀዋል።


 

የተገነቡት መሰረተ ልማቶች የአካባቢውን ሕብረተሰብ ዘመናት ያስቆጠሩ ጥያቄዎች የሚፈቱ መሆናቸውን የገለጹት የወረዳው አስተዳዳሪ፤ ሕዝቡ ለፕሮጀክቶቹ አስፈላጊውን እንክብካቤ በማድረግ ለመጪው ትውልድ ማስተላለፍ እንዳለበት አሳስበዋል።

ኢዜአ ያነጋገራቸው የኢሉ ገላን ወረዳ ነዋሪዎችም በአካባቢያቸው ለአገልግሎት የበቁ ፕሮጀክቶች የረጅም ጊዜ ጥያቄያቸውን ከመመለስ ባለፈ፣ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነታቸውን እንደሚያሳድጉት ያላቸውን እምነት ገልጸዋል።


 

አቶ ሁንዱማ ታረሳ "በቀበሌያችን የተገነባው ዲጂታል ቤተ መጻሕፍት አገልግሎት መጀመሩ የአካባቢው ተማሪዎች በቴክኖሎጂ ታግዘው ዕውቀት እንዲቀስሙና በሀገር አቀፍም ሆነ በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ ትልቅ እገዛ ያደርጋል" ብለዋል።


 

ወጣት ደራርቱ ወጋሪ በበኩሏ፤ ለአገልግሎት የበቁት መሰረተ ልማቶች የአካባቢውን ሕብረተሰብ ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ ከመሆናቸውም በላይ፣ ለወጣቶች ሰፊ የሥራ ዕድል የሚፈጥሩ በመሆናቸው ጠቀሜታው የጎላ መሆኑን ገልጻለች።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም