ዩኒቨርሲቲው ተመራቂ ተማሪዎች ስራ ፈጣሪ እንጂ ስራ ጠባቂ እንዳይሆኑ እየሰራ ነው - ኢዜአ አማርኛ
ዩኒቨርሲቲው ተመራቂ ተማሪዎች ስራ ፈጣሪ እንጂ ስራ ጠባቂ እንዳይሆኑ እየሰራ ነው
ባህር ዳር ፤ ሰኔ 18/2018 (ኢዜአ)፦ የባህር ዳር ዩኒቨርሲቲ በተግባር ተኮር ትምህርት ላይ በመመስረት ተመራቂ ተማሪዎች ስራ ፈጣሪ እንጂ ስራ ጠባቂ እንዳይሆኑ እየሰራ መሆኑን ገለጸ።
የዩኒቨርሲቲው ሴኔት ያዘጋጀውና ለሁለት ቀናት የሚቆየው "የስታርትአፕ፣ የቀጣሪ ድርጅቶችና የተመራቂዎች" ትስስር መድረክ ዛሬ መካሄድ ጀምሯል።
የባህር ዳር ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት መንገሻ አየነ (ዶ/ር) በመድረኩ እንዳሉት፤ ተመራቂዎች ሥራ ከመጠበቅ ይልቅ በፈጠራ ላይ ተመስርተው የራሳቸውን ድርጅት በመመሥረት ለሌሎች የሥራ ዕድል የሚፈጥሩ እንዲሆኑ በትኩረት እየተሠራ ነው።
ዩኒቨርሲቲው ካሉት 440 በላይ የትምህርት ፕሮግራሞች ውስጥ 70 በመቶ ያህሉ በድህረ-ምረቃ ደረጃ የሚሰጡ በመሆናቸው፣ ችግሮችን በምርምር ለመፍታትና ተወዳዳሪ ተመራቂዎችን ለማብዛት ምቹ ሁኔታ መፈጠሩን ተናግረዋል።
በዚህም ተማሪዎች ገና ሳይመረቁ የፈጠራ ሃሳባቸውን ወደ ተግባር ቀይረው ድርጅት በማቋቋም ሲወጡ ለሌሎች ተስፋ የሚሆኑ ተጨባጭ ውጤቶች እየተገኙ መሆኑን ገልጸዋል።
ለዚህ ስኬትም ዩኒቨርሲቲው አስፈላጊውን የበጀትና የሰው ኃይል በመመደብ እንዲሁም መሠረተ ልማትን በማሟላት ላይ አተኩሮ እየሠራ መሆኑን ጠቁመው፣ የዛሬው መድረክም ፈጣሪዎችንና ቀጣሪዎችን ለማገናኘት ያለመ ነው ብለዋል።
የባህር ዳር ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት ሳይንቲፊክ ዳይሬክተር ምትኩ ዳምጤ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ አሁን ላይ ተማሪዎች ተመርቀው ሲወጡ ከትምህርት ማስረጃ በተጨማሪ የፈጠራ ባለቤትነት (ፓተንት) ይዘው እየወጡ መሆኑን ገልጸዋል።
ይህ ውጤት ሊመዘገብ የቻለው ዩኒቨርሲቲው ባቋቋማቸው የቋንቋ፣ የሶፍት ስኪል እና የቢዝነስ ኢንኩቤሽን ማዕከላት አማካኝነት ተማሪዎች ክህሎታቸውን እንዲያዳብሩ በመደረጉ መሆኑን አረጋግጠዋል።
በዚህም የተቋሙ ምሩቃን እንደ ናሳ፣ ቦይንግ፣ ጎግልና አማዞን ባሉ ግዙፍ ዓለም አቀፍ ኩባንያዎች ውስጥ እየሠሩ እንደሚገኙ ጠቁመው፣ በክህሎት የዳበሩ ተማሪዎችን የማፍራት ተልዕኮው ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልጸዋል።
በዕለቱ የፈጠራ ሥራዎቻቸውን ካቀረቡት መካከል በዩኒቨርሲቲው የኬሚካል ኢንጂነሪንግ መምህርና ተመራማሪው ኢዮሲያስ አለሙ፤ ከድንች የእንጀራና የዳቦ ዱቄት በማዘጋጀት የተሳካ የፈጠራ ሥራ ማቅረባቸውን ገልጸዋል።
ፈጠራው ተገቢውን ዕውቅና ማግኘቱን ጠቅሰው፣ የድንች ዱቄትን በኪሎ 70 ብርና ከዚያ በታች በሆነ ዋጋ በማቅረብ አሁን የሚስተዋለውን የኑሮ ውድነት ለመቅረፍ የሚያስችል መሆኑን አስረድተዋል።
ሌላው የሜካኒካል ኢንጂነሪንግ ተመራቂ ዳግም ደጉ በበኩሉ፤ የከተሞችን የኮሪደር ልማት ዘመናዊነት የሚመጥን፣ በአንድ ጊዜ 30 ጫማዎችን ማጠብ የሚችል ማሽን ሠርቶ አቅርቧል።
በአሁኑ ወቅት ከአንድ ጓደኛው ጋር በመሆን ማሽኑን በትዕዛዝ አምርተው በማቅረብ ገቢ ማግኘት መጀመራቸውንና በቀጣይም ለሌሎች ወጣቶች የሥራ ዕድል ለመፍጠር መዘጋጀታቸውን ገልጿል።
ለሁለት ቀናት በሚቆየው በዚህ የስታርትአፕና የሥራ ፈጠራ መድረክ ላይ የዩኒቨርሲቲው ከፍተኛ አመራሮች፣ የሥራ ፈጣሪዎች፣ ተማሪዎችና የዩኒቨርሲቲው ማኅበረሰብ አባላት በመሳተፍ ላይ ይገኛሉ።