የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር በዶሮ፣ በወተት፣ በእንቁላል፣ በአሳና ሌሎች ምርት ልማት ላይ መሠረታዊ ለውጥ እያመጣ ነው - ኢዜአ አማርኛ
የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር በዶሮ፣ በወተት፣ በእንቁላል፣ በአሳና ሌሎች ምርት ልማት ላይ መሠረታዊ ለውጥ እያመጣ ነው
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 17/2018 (ኢዜአ)፦ የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር በዶሮ፣ በወተት፣ በእንቁላል፣ በአሳና በሌሎች ምርት ልማት ላይ መሠረታዊ ለውጥ እያመጣ መሆኑን የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ፍቅሩ ረጋሳ ገለጹ፡፡
ጥቅምት 23 ቀን 2015 ዓ.ም በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በይፋ በተጀመረው የሌማት ትሩፋት መርሐ-ግብር፣ ቀደም ሲል ትኩረት አጥቶ የነበረውን የእንስሳት ተዋጽኦ ልማት በቅንጅትና በቴክኖሎጂ በመደገፍ አሁን ላይ ተጨባጭ ውጤት እያስገኘ ይገኛል።
በዚህም መርሐ-ግብሩ የእንስሳት ተዋጽኦ ምርት እምርታን በተግባር በማሳየት የሀገሪቱን የምግብ ሉዓላዊነትና የዜጎችን ክብር ለማረጋገጥ የተጣለውን ግብ እያሳካ ይገኛል።
የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ፍቅሩ ረጋሳ፤ ኢትዮጵያ የምግብ ሉዓላዊነቷን ለማረጋገጥ የምታደርገውን ጥረት ለማሳካት የእንስሳት ሀብት ልማት ሚና ጉልህ መሆኑን ገልጸዋል።
በ2018 በጀት ዓመት የገበያ ፍላጎትን መነሻ በማድረግ የእንስሳት ምርታማነትንና ጤናን ለማጎልበት የዳልጋ ከብቶች ዝርያ ማሻሻልና ማዳቀል ሥራዎች በስፋት መከናወናቸውን አስታውቀዋል።
በዚህም 4 ነጥብ 9 ሚሊዮን የወተት ላሞችን ለማዳቀል የተያዘው እቅድ እየተሳካ ሲሆን፣ 160 ሚሊዮን ጫጩቶችን ለማሰራጨትና 11 ነጥብ 7 ቢሊዮን እንቁላል ለማምረት የተያዘው ግብም በውጤታማነት እየሄደ ይገኛል ብለዋል፡፡
ሚኒስቴሩ የዶሮ ምርትን ለማሳደግ 4 ዘመናዊ የጫጩት ማስፈልፈያ ማሽኖችን ለክልሎች ያሰራጨ ሲሆን፣ ተጨማሪ 11 ማሽኖችን ለመግዛት በሂደት ላይ እንደሚገኝም አብራርተዋል።
በተጨማሪም በኩሬዎችና በሰው ሠራሽ ሐይቆች የአሳ ምርት ልማት በስፋት እየተከናወነ እንደሚገኝ ገልጸዋል።
በበጀት ዓመቱ የእንስሳት ጤናን ለመጠበቅ አዳዲስ አሠራሮች፣ የተጠናከረ የክትባት ስርጭት እና የኤክስቴንሽን አገልግሎት በመዘርጋቱ ዘርፉን በተገቢው መንገድ ለማልማት የሚያስችል ትልቅ አቅም ተፈጥሯል ብለዋል።
በተለይም ወደ ውጭ የሚላኩ ምርቶች በሚገኙባቸው የአርብቶ አደር አካባቢዎች የድንበር ዘለል በሽታዎችን ለመቆጣጠር ክትባት በስፋት መሰጠት የተጀመረ ሲሆን፣ ከጎረቤት ሀገራት ጋር በጋራ የመሥራት ባህልም እያደገ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡
ባለፉት ዓመታት በሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር የተከናወኑ ተግባራት የእንስሳትን ምርታማነትን በከፍተኛ ደረጃ ማላቃቸውን ገልጸዋል።
ለዚህም ማሳያ የሚሆነው በሀገሪቱ የነበረው የእንቁላል ማምረት አቅም በዓመት ከ3 ነጥብ 2 ቢሊዮን ወደ 11 ነጥብ 7 ቢሊዮን፣ የወተት ምርት ደግሞ በዓመት ከ7 ነጥብ 1 ቢሊዮን ወደ 16 ቢሊዮን ሊትር ማደጉን ለአብነት ጠቅሰዋል፡፡
እነዚህ ስኬቶች ኢትዮጵያ የምግብ ሉዓላዊነቷን ማረጋገጥ ያስቀመጠችውን ግብ ለማፋጠን ትልቅ አቅም መፍጠራቸውንም አስረድተዋል።
የእንስሳት ምርታማነትን በዘላቂነት ለማስቀጠል የመኖ አቅርቦትን ለማሻሻል እየተሰራ መሆኑን የገለጹ ሲሆን ማሽኖችን ገዝቶ ለክልሎች ማሰራጨቱንና የግሉ ዘርፍ ፋብሪካዎችም እገዛ እያደረጉ መሆኑን ገልጸዋል።