ኢትዮጵያ አስተማማኝ እና ሁሉን አቀፍ የዲጂታል መጻኢ ዕድልን ለመገንባት በቁርጠኝነት እየሠራች ነው - ኢዜአ አማርኛ
ኢትዮጵያ አስተማማኝ እና ሁሉን አቀፍ የዲጂታል መጻኢ ዕድልን ለመገንባት በቁርጠኝነት እየሠራች ነው
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 17/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ አስተማማኝ እና ሁሉን አቀፍ የዲጂታል መጻኢ ዕድልን ለመገንባት በቁርጠኝነት እየሠራች መሆኑን የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ዋና ዳይሬክተር ትዕግስት ሃሚድ ገለጹ።
በሳይበር ደህንነት እና በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ (AI) ላይ ያተኮረና ለሁለት ቀናት የሚቆይ ዓለም አቀፍ ጉባኤ ዛሬ በአዲስ አበባ መካሄድ ጀምሯል።
የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ዋና ዳይሬክተር ትዕግስት ሃሚድ እንደገለጹት፤ ኢትዮጵያ በ"ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030" ስትራቴጂ እየተመራች በዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ጉዞዋ ላይ አዲስና ተስፋ ሰጪ ምዕራፍ ላይ ትገኛለች።
ቴክኖሎጂ ለሀገራዊ ልማት መሠረታዊ አጋዥ ተደርጎ እየተወሰደ እንደሚገኝም አብራርተው፤ ደህንነቱ የተጠበቀ የዲጂታል ሥነ-ምህዳር የቴክኖሎጂ አስፈላጊነት ብቻ ሳይሆን የሀገር ሉዓላዊነት፣ የኢኮኖሚ ጥንካሬ እና የዘላቂ ልማት መሠረታዊ ምሰሶ መሆኑንም ገልጸዋል።
የዲጂታል ቴክኖሎጂዎች የግብርና ዘመናዊነትን እያፋጠኑ፣ የፋይናንስ ቴክኖሎጂ አቅምን እያሰፉ፣ የሀገር ውስጥ የፈጠራ ሥነ-ምህዳርንና የቴክኖሎጂ ኢንተርፕራይዞችን ከመደገፍ ባሻገር ወሳኝ የዲጂታል ሥርዓቶችን በራስ የማልማት ብሔራዊ አቅምን እያጠናከሩ መሆኑን ጠቁመዋል።
የአህጉሪቱን የዲጂታል መጻኢ ጉዞ ለማረጋገጥም በሳይበር ደህንነት፣ በትምህርት፣ በላቀ ቴክኒክ ሥልጠና፣ በምርምርና ፈጠራ እንዲሁም በወጣቶች ተሰጥኦ ማልማት ላይ ከፍተኛ ኢንቨስትመንት እየተደረገ እንደሚገኝ አስታውቀዋል።
ኢትዮጵያ የሳይበር ደህንነት ትብብርን ለማሳደግ፣ ኃላፊነት የተሞላበት ፈጠራን ለማበረታታት፣ የአቅም ግንባታን ለማጠናከር እና የመረጃ ልውውጥን ለማመቻቸት ከመንግሥታት፣ ከአለም አቀፍ ድርጅቶች፣ ከአካዳሚክ ማኅበረሰብ እና ከኢንዱስትሪ መሪዎች ጋር በቅንጅት እየሠራች መሆኑን አስረድተዋል።
የኢትዮጵያ የሳይበር ደህንነት ማኅበር ፕሬዚዳንት ብርሃኔ በየነ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ኮንፈረንሱ የአፍሪካን የሳይበር ደህንነት አቅምና የዳታ ሉዓላዊነትን ለማጠናከር እንዲሁም የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ አጠቃቀምን ለማበረታታት ያለመ መሆኑን ገልጸዋል።
የአፍሪካን የሳይበር ደህንነት አቅምን ማሳደግ እንደሚገባ ጠቅሰው፤ በዘርፉ ያሉ የክህሎትና የአቅም ክፍተቶችን መለየት የጉባኤው ዋነኛ ትኩረት መሆኑን ተናግረዋል።
በአፍሪካ ቀጣናዊ ትብብርን በመገንባት ደህንነቱ የተጠበቀ የዲጂታል ትራንስፎርሜሽንና አርቲፊሻል ኢንተለጀንስን ማረጋገጥ ወሳኝ መሆኑን ጠቁመው፣ ይህ መድረክ ለእውቀት ሽግግርና ለተግባራዊ የመፍትሄ ሐሳቦች መፈጠር ትልቅ እገዛ እንደሚያደርግ ገልጸዋል።
የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን (ECA) የፕሮግራም ድጋፍ ምክትል ዋና ጸሐፊ ማማ ኬይታ በበኩላቸው፤ አፍሪካ ያሏትን ምቹ ሁኔታዎች ወደ ዘላቂ የዲጂታል መፍትሄዎች የመቀየር ታሪካዊ ዕድል እንዳላት ገልጸዋል።
አህጉሪቱ የቴክኖሎጂ ተጠቃሚ ብቻ ከመሆን ወጥታ የወደፊት ዕጣ ፈንታዋን በራሷ መቅረጽ የምትችለው የዲጂታል ሽግግርን እና የፈጠራ ሥነ-ምህዳሮችን በቁርጠኝነት ስትደግፍ መሆኑን አስገንዝበዋል።
ለዚህም ስኬት ጠንካራ ፖሊሲዎችን መቅረጽ፣ አዳዲስ ተነሳሽነቶችን መጀመር፣ ኢንቨስትመንቶችን ማንቀሳቀስ እና የተጀመሩ የተቀናጀ የጋራ ቁርጠኝነት ሊጠናከሩ ይገባል ብለዋል፡፡