ቀጥታ፡

በነቀምቴ ከተማ ህብረተሰቡ ለሰላምና ልማት መጠናከር ባሳየው ቁርጠኝነት ስኬታማ ሥራዎች ተከናውነዋል

ነቀምቴ፤ ሰኔ 16/2018 (ኢዜአ)፦ በነቀምቴ ከተማ ህብረተሰቡ ለሰላምና ልማት መጠናከር ባሳየው ቁርጠኝነት በርካታ የልማት ሥራዎች መከናወናቸውን የኦሮሚያ ክልል ፀጥታ እና አስተዳደር ቢሮ ኃላፊ ኮሚሽነር አራርሳ መርዳሳ ገለጹ።

በነቀምቴ ከተማ በ189 ሚሊየን ብር ወጪ የተገነቡ ሼዶች ዛሬ ተመርቀዋል።


 

በሼዶቹ ምረቃ ላይ የኦሮሚያ ክልል ፀጥታ እና አስተዳደር ቢሮ ኃላፊ ኮሚሽነር አራርሳ መርዳሳ፣ የክልሉ ሲቪል ሰርቪስና የሰው ሀብት ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ ኮከቤ ዲዳ፣ የነቀምቴ ከተማ ከንቲባ መሰረት ሀይሉ እና ሌሎች የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል።

ኮሚሽነር አራርሳ መርዳሳ የከተማውንና አካባቢውን ሰላም ለማጠናከር ህብረተሰቡን ከፀጥታ አካላት ጋር በማስተባበር በተሰራው ሥራ የአካባቢው ሰላም ማጠናከርና የልማት ሥራዎችን በስፋት ማከናወን መቻሉን ተናግረዋል።

በተለይ ለከተማው ወጣቶች የሥራ አማራጭ እየተመቻቸ መሆኑን ጠቅሰው፤ ወጣቶችም የሥራ ዕድሉን በአግባቡ በመጠቀም ከራሳቸው አልፈው ለሌሎች መትረፍ እንዳለባቸው አስገንዝበዋል።

የነቀምቴ ከተማ ከንቲባ መሰረት ሀይሉ በበኩላቸው በከተማዋ ሰፊ የልማት ስራዎች እየተከናወኑ መሆናቸውን ገልፀዋል።


 

ማህበረሰቡ ለሰላሙ ዘብ ቆሞ ለልማት ባሳየው ቁርጠኝነት የተጀመሩ የልማት ሥራዎች በተያዘላቸው የጊዜ ገደብ ተጠናቀው ለአገልግሎት እየበቁ መሆኑን ተናግረዋል።

ዛሬ ተመርቀው ለአገልግሎት በበቁት ሼዶችም ወጣቶች ሰርተው ራሳቸውን እንዲለውጡ ለማስቻል የከተማዋ አስተዳደሩ የቅርብ ክትትልና ድጋፍ ያደርጋል ብለዋል።

የነቀምቴ ከተማ አስተዳደር ማዘጋጃ ቤት ኃላፊ አቶ ቶለሳ ደጋጎ ዛሬ ለምረቃ የበቁት ሼዶች በመንግሥት 189 ሚሊዮን ብር ወጪ የተደረገባቸው መሆኑን ተናግረዋል።


 

ሼዶቹም በ104 ማህበራት ለተደራጁ 520 ወጣቶች የሥራ ዕድል ለመፍጠር የሚያስችሉ መሆኑን ገልጸው፤ ወጣቶቹም በከብት ማድለብ፣ በሥጋና እንቁላል ዶሮ እርባታ፣ በወተት ልማትና በመሰል የሥራ ዘርፎች የተደራጁ ናቸው ብለዋል።

የሥራ ዕድል ከተፈጠረላቸው ወጣቶች መካከል ወጣት ሙሉጌታ መልካሙ ከጓደኞቹ ጋር በወተት ምርት በመደራጀት በአምስት ሚሊየን ብር ካፒታል ሥራ ለመጀመር መዘጋጀታቸውንም ተናግሯል።


 

የከተማ አስተዳደሩ ያመቻቸላቸውን እድል በመጠቀም ሰርተው ራሳቸውን ለመለወጥ ማቀዳቸውን ተናግሯል።

ሌላኛው የሥራ እድል ተጠቃሚ ወጣት ቢቂላ ለማ በበኩሉ ከብት በማድለብ ሥራ ላይ ለመሰማራት እንደተደራጁ ገልጾ፤ በስራቸው ውጤታማ ለመሆን ተግተው እንደሚሰሩ አመልክቷል።

መንግስት ያመቻቸውን የሥራ እድል በመጠቀም ሰርቶ ለመለወጥ ቁርጠኛ መሆኑንም አረጋግጧል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም