የኢትዮጵያ የግብርና ዘርፍ ከእጅ ወደ አፍ ልምምድ ተላቆ ወደ ንግድና የሉዓላዊነት መሠረት ተሸጋግሯል - ኢዜአ አማርኛ
የኢትዮጵያ የግብርና ዘርፍ ከእጅ ወደ አፍ ልምምድ ተላቆ ወደ ንግድና የሉዓላዊነት መሠረት ተሸጋግሯል
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 16/2018 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ የግብርና ዘርፍ ከእጅ ወደ አፍ ልምምድ ተላቆ ወደ ንግድና የሉዓላዊነት መሠረት ሽግግር ማድረጉን የግብርና ትራንስፎሜሽን ኢንስትቲዩት ዋና ሥራ አስፈፃሚ ማንደፍሮ ንጉሴ (ዶ/ር) አመለከቱ።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በተገኙበት “ከለውጥ ወደ ዘላቂ ሽግግር” በሚል መሪ ቃል የ“ኢትዮጵያ ታከናውናለች” ጉባኤ እየተካሄደ ይገኛል።
የግብርና ትራንስፎሜሽን ኢንስትቲዩት ዋና ሥራ አስፈፃሚ ማንደፍሮ ንጉሴ (ዶ/ር) በጉባኤው ላይ የግብርና ዘርፍ የለውጥ ጉዞን በተመለከተ ማብራሪያ ሰጥተዋል።
በማብራሪያቸውም ኢትዮጵያ ስልታዊ ኢንቨስትመንቶችን እና ጉልህ ማሻሻያዎችን በማከናውን የሀገሪቱን የግብርና ዘርፍ ከነበረበት ከእጅ ወደ አፍ ልምምድ ተላቃ አሁን ላይ ከእርሻ ወደ ንግድ ብሎም የሉዓላዊነት መሰረት የተሸጋገረ መሆኑን አመላክተዋል።
ለዚህም ከ10 ዓመቱ መሪ እቅድ ጋር የተጣጣሙ ስትራቴጂዎችንና የፖሊሲ ለውጦ ማዕቀፎችን በመንደፍ፤ የመንግሥት፣ የግል ዘርፉንና የህዝብ አጋርነትን በማጠናከር፣ ፈጠራንና የግብርና ቢዝነስን በማስፋፋት እንዲሁም የምግብ ሉዓላዊነትን በማሳደግ የግብርናው ዘርፍ ይበልጥ ምርታማ፣ በገበያ ላይ የተመሰረተ እና ተፈጥሮአዊና ሰው ሰራሽ ቀውሶችን የመቋቋም አቅሙ የዳበረ እንደሆነ ገልጸዋል።
ቀደም ሲል ከውጪ በሚገቡ ምርቶች ላይ በስፋት ተመርኩዛ የነበረችው ኢትዮጵያ አሁን ላይ በሀገር ውስጥ ተተኪ ምርቶችን በማሳደግ፣ የሌማት ትሩፋትና መሰል ሀገር በቀል ተነሳሽነቶችን በማዳበር፣ ቴክኖሎጂንና የሰው ሰራሽ አስተውሎትን በመታገዝ ለወጣቱ የስራ እድልን ከመፍጠር ባሻገር ሀገሪቱ በምግብ ራሷን ለመቻል ለምታደርገው ጉዞ አመርቂ ውጤት እያስገኘ እንደሚገኝ ዋና ሥራ አስፈፃሚው አስታውቀዋል።
እነዚህ የታቀዱና መጻኢውን ጊዜ ያገናዘቡ ስልታዊ እርምጃዎች ለዘላቂ የግብርና አብዮት፣ ለገጠር ብልጽግና እና ለጠንካራ ኢኮኖሚ መሰረት እየጣሉ ሲሆን ይህም ኢትዮጵያ ወደፊት እየተራመደችና ተጨባጭ ለውጥ እያስመዘገበች መሆኑን በተግባር እንደሚያሳይ አመልክተዋል።