ቀጥታ፡

ስንዴን በኩታ ገጠም በማልማታችን ኑሯችን እየተሻሻለ መጥቷል-  አርሶ አደሮች 

አምቦ፤ ሰኔ 15/2018 (ኢዜአ)፦ ስንዴን በኩታ ገጠም ማልማት ከጀመሩ ወዲህ ኑሯቸው እየተሻሻለ መምጣቱን በምዕራብ ሸዋ ዞን የወልመራ ወረዳ አርሶአደሮች ተናገሩ፡፡

በዞኑ ወልመራ ወረዳ የመኸር ኩታ ገጠም ስንዴ ልማት ዘር ማስጀመሪያ መርሃ ግብር የዞኑ እና የወረዳው የስራ ሀላፊዎች በተገኙበት ተካሄዷል፡፡

በወቅቱ ኢዜአ ያነጋገራቸው የወረዳው አርሶአደሮች ባለፉ ዓመታት ስንዴን በኩታ ገጠም በማልማት ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸው እያደገ መምጣታቸውን ገልጸዋል፡፡

ከአርሶ አደሮቹ መካከል ነገሰ ለታ እንደገለጹት ባለፉት ሶስት ዓመታት ከአካባቢው አርሶ አደሮች ጋር በመደራጀት በኩታ ገጠም ስንዴን እያለሙ ነው፡፡

ስንዴን በኩታ ገጠም ማልማታቸው ከዚህ በፊት ከአንድ ሄክታር ያገኙት የነበረውን 20 ኩንታል ምርት አሁን ላይ ወደ 40 ኩንታል ማድረስ እንደቻሉ ተናግረዋል።

የስንዴን ምርታማነት ለማሳደግም ግብአትን በአግባቡ መጠቀምና ከወረዳው ግብርና ጽህፈት ቤት ባለሙያዎች ሙያዊ ድጋፍ ማግኘታቸውን ጠቁመዋል።

ሌላው አርሶ አደር ደንደና ከበደ በበኩላቸው በመኸር እርሻ ከስንዴ ልማታቸው የተሻለ ምርት ለማግኘት በኩታ ገጠም ማረሳቸውን ተናግርዋል።

የባለፉት አመታት የኩታገጠም እርሻ የተሻለ ምርት ለማግኘት እንደረዳቸው ጠቁመው ዘንድሮም ተግባሩን ለማስቀጠል እየተጉ መሆናቸውን ገልጸዋል ።

ከአካባቢያቸው አርሶአደሮች ጋር በኩታ ገጠም ማረሳቸው ከኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸው ባለፈ በማህበራዊ ኑሯቸው ላይም ለውጥ ማምጣቱን አስረድተዋል፡፡

የወረዳው ግብርና ጽፈት ቤት የግብርና ግብአት በወቅቱ ማቅረቡም ለምርታማነታቸው ማገዙን ጠቅሰዋል።

የወልመራ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዲዳ ጋሪ በበኩላቸው፤ በወረዳው የአርሶአደሮችን ምርታማነት በማሳደግ ከተረጅነት ለማውጣት በቅንጅት መሰራቱን ጠቁመዋል።

ለዚህም ለአርሶ አደሩ ግብአትና ሙያዊ ድጋፍን በማቅረብ በምግብ ራስን ከመቻል አልፎ የቁጣባ ባህሉ እያደገ መምጣቱን ገልጸዋል፡፡

በዘንድሮ መኸር እርሻ በወረዳው ከ34 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች ለማልማት ከታቀደው ውስጥ 18 ሺህ ሄክታሩ በስንዴ እንደሚለማ ተናግረዋል።

ከስንዴ ልማቱም 900 ሺህ ኩንታል ምርት ለማገኘት ታቅዶ እየተሰራ ነው ብለዋል፡፡

የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ መርጋ አየለ፤ በዞኑ በመኸር እርሻ ከ900 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች ለመሸፈን ታቅዷል ብለዋል።
 
በመኸር አዝመራው በቆሎ፣ ማሽላ እና ስንዴ በኩታ ገጠም እንደሚለሙ ጠቁመው  ከዚህም ውስጥ  ከ232 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በስንዴ ለማልማት መታቀዱን  ተናግረዋል፡፡

መንግሥት ለግብርናው ዘርፍ በሰጠው ትኩረት የአርሶ አደሩን  ምርትና ምርታማነት ማሳድግ መቻሉን የገለጹት ደግም የዞኑ ምክትል አስተዳዳሪ አቶ አበበ ጨመዳ ናቸው።

 
የግብርናውን ውጤታማነት ለማሳደግ ለግብርና ቴክኖሎጂና ግብአት አቅርቦት ትኩረት መሰጠቱን አንስተዋል።

የአርሶ አደሩን የኩታ ገጠም አስተራረስ ግንዛቤ በማጎልበት ምርታማነቱን በማሳድግ ከፍጆታው አልፎ ለገበያ የሚያቀርብበትን አቅም ለመፍጠር  እየተሰራ መሆኑን  አስታውቀዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም