ፋውንዴሽኑ ከመንግሥት ተቋማት ጋር በመቀናጀት ለስራ ፈጣሪ ወጣቶች ድጋፍ እያደረገ ነው - ኢዜአ አማርኛ
ፋውንዴሽኑ ከመንግሥት ተቋማት ጋር በመቀናጀት ለስራ ፈጣሪ ወጣቶች ድጋፍ እያደረገ ነው
ጂንካ፤ሰኔ 15/2018(ኢዜአ) ፡-የኃይለማርያምና ሮማን ፋውንዴሽን ከመንግሥት ተቋማት ጋር በመቀናጀት በሚያደርግላቸው ድጋፍ ተጠቃሚ መሆናቸውን በደቡብ ኦሞ እና በአሪ ዞኖች የሚገኙ ስራ ፈጣሪ ወጣቶች ተናገሩ።
ፋውንዴሽኑ ከማስተር ካርድ ፋውንዴሽን እና ከመንግስታዊ ተቋማት ጋር በመቀናጀት በወጣቶች የኢኮኖሚ አቅም ግንባታ ላይ ያከናወናቸውን ተግባራት አስመልክቷል።
በጂንካ ዩኒቨርሲቲ በተካሄደው ኤግዚቢሽን ላይ ስራዎቻቸውን ያቀረቡ ስራ ፈጣሪ ወጣቶችም የኃይለማርያምና ሮማን ፋውንዴሽን ከመንግሥት ተቋማት ጋር በመቀናጀት በሚያደርጉላቸው ድጋፎች ተጠቃሚ መሆን መጀመራቸውን ገልጸዋል።
በአሪ ዞን የደቡብ አሪ ወረዳ ነዋሪ ወጣት ያዕቆብ ገርሲኖ በፋውንዴሽኑ እና በመንግሥት ተቋማት ድጋፍ 10 አባላት ያሉት ማህበር በማቋቋም በንብ ማነብ ስራ እንደተሰማሩ ገልጿል።
በአሪ ዞን ጂንካ ከተማ በዶሮ እርባታ ከተሰማሩ ወጣቶች መካከል ወጣት ወንድምነህ ሀብታሙ እንደገለፀው 10 አባላት ያለው ማህበር በማቋቋም በ45 ቀን ጫጩት አቅርቦት እና በዕንቁላል ጣይ ዶሮ እርባታ መሰማራታቸውን ጠቁሟል።
ፋውንዴሽኑ እና መንግስታዊ ተቋማት ድጋፍ በዶሮ እርባታ በቂ ስልጠና መውሰዳቸውን ጠቁመው ፥ አሁን ላይ እስከ 4 ሺህ ጫጩቶችን ለገበያ በማቅረብ ጥሩ ገቢ እያገኙ መሆናቸውን ተናግሯል።
ሌላው በደቡብ ኦሞ ዞን ሐመር ወረዳ ወጣት ሉቲየ ወንጌላ በበኩሉ 10 አባላት ያለው ማህበር በማቋቋም ፍየል በማሞከት ለገበያ የማቅረብ ስራ ላይ መሰማራታቸውን ገልጿል።
በወሰዱት በቂ ስልጠናና እና ድጋፍ ፍየሎችን በማድለብና ለገበያ በማቅረብ የተሻለ ገቢ እያገኘ መሆኑንም ጠቁመዋል ።
የፋውንዴሽኑ ምክትል ዋና ስራ አስፈፃሚ ሶስና ኃይለማርያም (ዶ/ር) በወቅቱ እንደገለፁት የኃይለማርያም እና ሮማን ፋውንዴሽን ከመንግስታዊ ካልሆኑ ተቋማትና ከመንግስታዊ ተቋማት ጋር በመተባበር በደቡብ ኦሞ እና በአሪ ዞኖች በተመረጡ ወረዳዎች የወጣቶች የራስ ስራ ፈጠራ ፕሮጀክት ተግባራዊ እያደረገ ነው።
የዚህ ፕሮጀክት ዓላማ ሥራ ፈላጊ ወጣቶችን በክህሎት ስልጠናዎች ማብቃት፣ ኢንተርፕራይዞችን እንዲያቋቁሙ መደገፍ፣ የፋይናንስ አቅርቦትን ማመቻቸት መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡
እንዲሁም ቀጣይነት ያለው የገበያ ትስስርና ተቋማዊ ድጋፍ እንዲኖር በማስቻል መንግስት ለወጣቶች የስራ ዕድል ለማመቻቸት እና የወጣቶችን የኢኮኖሚ አቅም ለማጎልበት እያደረገ ያለውን ጥረት ማገዝ እንደሆነ ገልጸዋል።
ላለፉት ሁለት ዓመታት በየደረጃው ከሚገኙ መንግስታዊ መዋቅሮችና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር በመቀናጀት በሁለቱ ዞኖች 31 ሺህ 617 ወጣቶችን በንግድ ክህሎት ስልጠና በመስጠት የማብቃት ስራ መስራቱን አንስተዋል።
የአሪ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አብርሃም አታ በበኩላቸው ፋውንዴሽኑን በዞኑ የሚገኙ ስራ ፈጣሪ ወጣቶችን የክህሎት እና የፋይናንስ አቅም በማጎልበት ትልቅ እገዛ እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል።
መንግስት የወጣቶችን ተጠቃሚነት ለማሳደግ ሰፊ ርብርብ እያደረገ መሆኑን ጠቅሰው፥ የፋውንዴሽኑ ድጋፍም ወጣቶቹ ውጤታማ እንዲሆኑ አቅምን ይፈጥራል ብለዋል።
የደቡብ ኦሞ ዞን ምክትል አስተዳዳሪ አቶ ታደለ ጋያ በበኩላቸው ፋውንዴሽኑ በአርብቶ አደሩ አካባቢ የተለያዩ ፕሮጀክቶችን በመቅረፅ የአርብቶ አደሩን ማህበረሰብ ተጠቃሚ እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል።
ፋውንዴሽኑ የወጣቶችን አቅም ከማጎልበት ባሻገር ተማሪዎችን የምገባ መርሃ ግብር በመደገፍ፣ ዘመናዊ እርሻን በማስተዋወቅ፣ በተፈጥሮ አያያዝና እንክብካቤ ረገድ ግንዛቤ በመፍጠር በጤናው ዘርፍ አስተዋጽኦ ማበርከቱን ገልጸዋል።