ቀጥታ፡

በሀገሪቱ የተጀመሩ የልማት ፕሮጀክቶችን ማስቀጠልና ማጠናቀቅ፣ ከብልጽግና ፓርቲ የሚጠበቅ ታሪካዊ ኃላፊነት ነው

ጅግጅጋ፤ ሰኔ 15/2018 (ኢዜአ)፦ በሀገሪቱ የተጀመሩ የልማት ፕሮጀክቶችን ማስቀጠልና ማጠናቀቅ፣ ከብልጽግና ፓርቲ የሚጠበቅ ታሪካዊ ኃላፊነት ነው ሲሉ የጅግጅጋ ከተማ ነዋሪዎች ገለጹ።

በ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ በሕዝብ ተወካዮች እና የክልል ምክር ቤቶች ብልጽግና ፓርቲ አብላጫውን መቀመጫ በማግኘት ማሸነፉን የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ አስታውቋል።

የምርጫውን ውጤት ይፋ መሆን በማስመልከት ኢዜአ ያነጋገራቸው የጅግጅጋ ከተማ ነዋሪዎች፤ ብልጽግና ፓርቲ የሕዝቡን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ የልማት ሥራዎችን አጠናክሮ ማስቀጠል እንዳለበት ገልጸዋል። 

ነዋሪዎቹ አክለውም፤ ለሀገሪቱ ዕድገትና ልማት መጎልበት ሕዝቡም ከፓርቲው ጎን በመቆም የድርሻውን ማበርከት እንዳለበት ተናግረዋል።

ከአስተያየት ሰጪዎቹ መካከል አቶ አደን ዩሱፍ እንደተናገሩት፤ በተለያዩ ዘርፎች የተመዘገቡትን የለውጥ ውጤቶች ማስቀጠል የአሸናፊው ፓርቲ ሃላፊነት ነው። 

ለውጦቹን በመደገፍም ለሀገራቸው ልማት የበኩላቸውን ኃላፊነት ለመወጣት ዝግጁ መሆናቸውን ገልጸዋል።

ሌላኛው ነዋሪ አቶ መሀመድ አብዲ በበኩላቸው፤ መንግሥት ባለፉት አምስት ዓመታት ሲያከናውናቸው የነበሩ የልማት ሥራዎችን የበለጠ ማጠናከር እንዳለበት ገልጸዋል። 

በተለይም በግብርናው ዘርፍ የተሰጠው ትኩረት የምግብ ሉዓላዊነትን የሚያረጋግጥና በምግብ ራስን ለመቻል የሚያስችል በመሆኑ፣ በቀጣይም ለዘርፉ ልዩ ትኩረት ሊሰጠው እንደሚገባ አሳስበዋል።

ፓርቲው በውኃ ተደራሽነት፣ በከተሞች መሠረተ-ልማት ማስፋፋትና የኑሮ ውድነትን በመቀነስ ረገድም የሕብረተሰቡን ተጠቃሚነት ማዕከል አድርጎ መሥራት እንዳለበት አክለው ገልጸዋል።

በሀገሪቱ የተጀመሩ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶች በፍጥነት ተጠናቀው ለአገልግሎትና ለምርታማነት እንዲበቁ በትኩረት መሥራት እንደሚያስፈልግ የገለጸው ደግሞ ወጣት አህመድ ኢብራሂም ነው።

የመንግሥት ሠራተኞችን ተጠቃሚነት ማሳደግና የተለያዩ ሥልጠናዎችን በመስጠት አቅማቸውን በማጎልበት፣ የአገልግሎት አሰጣጥን ማሻሻል እንደሚገባም ገልጿል።

ነዋሪዎቹ የመንግሥትን የልማት ጥረቶች በመደገፍና የልማት ሥራዎች እንዲጠናከሩ በማድረግ ረገድ የበኩላቸውን ድርሻ ለመወጣት ዝግጁ መሆናቸውን ገልጸዋል።

የ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ የመጨረሻ ውጤት ይፋ መሆኑን ተከትሎ አሸናፊ የሆነው ብልፅግና ፓርቲ ለመላው የኢትዮጵያ ህዝብ ምስጋና አቅርቧል።

በመልእክቱም በአጠቃላይ ብልፅግና ፓርቲ የገባውን ቃል ሳይሸራረፍ በመተግበር፣ ምርጫ የሥልጣን መቆናጠጫ ሳይሆን ሕዝብን በቅንነትና በታማኝነት ማገልገያ ታላቅ አደራ መሆኑን ገልጿል።

በመሆኑም የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ ብልፅግና በተግባር የማረጋገጥ ታሪካዊ ጉዟችንን ከምንጊዜውም በላይ በበለጠ ትጋት፣ አንድነትና ቁርጠኝነት አጠናክረን ለመቀጠል ለተከበረው ሕዝባችን ዳግም ቃላችንን እናድሳለን ሲል ማረጋገጡ ይታወሳል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም