የኢትዮጵያ የተቀማጭ ገንዘብ መድን ፈንድ ከተቋቋመ ጀምሮ ከአባል የፋይናንስ ተቋማት 20 ነጥብ 61 ቢሊየን ብር አረቦን ሰብስቧል - ኢዜአ አማርኛ
የኢትዮጵያ የተቀማጭ ገንዘብ መድን ፈንድ ከተቋቋመ ጀምሮ ከአባል የፋይናንስ ተቋማት 20 ነጥብ 61 ቢሊየን ብር አረቦን ሰብስቧል
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 9/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የተቀማጭ ገንዘብ መድን ፈንድ ከተቋቋመ ጀምሮ ከአባል የፋይናንስ ተቋማት 20 ነጥብ 61 ቢሊየን ብር አረቦን መሰብሰቡን የፈንዱ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ደሳለኝ አምባው (ዶ/ር) አስታወቁ፡፡
የፈንዱ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ደሳለኝ አምባው (ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የመድን ፈንዱ በተቋቋመ አጭር ዓመታት ውስጥ ለአባል የፋይናንስ ተቋማት አማራጭና ውጤታማ የፋይናንስ ሥርዓት ፈጥሯል።
ከአባል ፋይናንስ ተቋማት አርቦን መሰብሰብ፣ የተሰበሰበን አርቦን በመንግስት ግምጃ ቤት ሰነድ ኢንቨስትመንትን ማሳደግና አንድ የፋይናንስ ተቋም ቢወድቅ ተቋሙን በመተካት ለገንዘብ አስቀማጮች ከ90 ቀናት ባነሰ ጊዜ መክፈል የሚያስችሉ ዋና ዋና ተግባራት መከናወናቸውን ገልጸዋል።
በዚህም የኢትዮጵያ ንግድ ባንክን ጨምሮ ከኢትዮጵያ ልማት ባንክ ውጭ ሁሉም የግል ባንኮችና ሁሉም የማይክሮ ፋይናንስ ተቋማት የኢትዮጵያ የተቀማጭ ገንዘብ መድን ፈንድ አባል መሆናቸውን ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ የተቀማጭ ገንዘብ መድን ፈንድ ከተቋቋመ ጀምሮ እስካሁን ባለው ከአባል የፋይናንስ ተቋማት 20 ነጥብ 61 ቢሊየን ብር አረቦን መሰብሰቡን አስታውቀዋል።
ከዚህ ውስጥ 18 ነጥብ 72 ቢሊዮን ብር ከመደበኛ ተቀማጭ ገንዘብ የተሰበሰበ ሲሆን፤ ቀሪው 1 ነጥብ 89 ቢሊዮን ብር ደግሞ ከወለድ ነጻ ተቀማጭ ገንዘብ የተሰበሰበ መሆኑን አስረድተዋል።
የፈንዱ አጠቃላይ የኢንቨስትመንት ክምችትም ካለፈው ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የ89 ነጥብ 76 በመቶ ብልጫ በማሳየት 22 ነጥብ 98 ቢሊየን ብር መድረሱን አንስተዋል።
ከጠቅላላ ኢንቨስትመንቱ 20 ነጥብ 97 ቢሊየን ብር በመንግሥት ግምጃ ቤት ሰነድ ላይ ውሏል፤ ቀሪው 2 ነጥብ 01 ቢሊየን ብር ደግሞ በሙዳራባህ የቁጠባ ኢንቨስትመንት ሂሳብ መቀመጡን አስታውቀዋል።
በ2018 በጀት ዓመት 9 ነጥብ 35 ቢሊየን ብር ለመሰብሰብ በታቀደው መሠረት፤ እስካለፈው ዘጠኝ ወር 6 ነጥብ 76 ቢሊየን ብር መሰብሰብ መቻሉን ተናግረዋል።
በኢትዮጵያ የተቀማጭ ገንዘብ መድን ፈንድ የተሰበሰበውን አርቦንም በአግባቡ ኢንቨስትመንት ላይ በማዋል የፋይናንስ ተቋማትን ጤናማነትና ተወዳዳሪነት የሚያጎለብት አቅም እየተገነባ መሆኑን ጠቅሰዋል።
የኢትዮጵያ የተቀማጭ ገንዘብ መድን ፈንድ ተጠሪነቱን ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ በማድረግ በሚኒስትሮች ምክር ቤት ደንብ ቁጥር 482/2013 መቋቋሙ ይታወሳል።
የኢትዮጵያ የተቀማጭ ገንዘብ መድን ፈንድ ከብሔራዊ ባንክ፣ ከኢትዮጵያ ባንኮች ማኅበርና ከኢትዮጵያ የማይክሮ ፋይናንስ ማኅበር በተውጣጡ አምስት የዳይሬክተሮች ቦርድ የሚመራ ተቋም ነው።