ቀጥታ፡

ኮርፖሬሽኑ በደቡብ ሱዳን የቤት ልማት ዘርፍ የተሰማራው አብሮነትን መርኅ አድርጎ ነው - ረሻድ ከማል (ዶ/ር)

አዲስ አበባ፤ ሰኔ 9/2018 (ኢዜአ)፡-የፌደራል ቤቶች ኮርፖሬሽን በደቡብ ሱዳን የቤት ልማት ዘርፍ የተሰማራው የጋራ ተጠቃሚነትን፣ አብሮነትን እና ወንድማማችነትን መርኅ አድርጎ መሆኑን የኮርፖሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ረሻድ ከማል (ዶ/ር) አስገነዘቡ።

ኮርፖሬሽኑ የመኖሪያና የንግድ ቤቶችን ለመገንባት የሚያስችለውን ስምምነት ማድረጉን ተከትሎ፤ የደቡብ ሱዳን መንግሥት የፌዴራል ቤቶች ኮርፖሬሽን በጁባ ከተማ ለሚያከናውነው የዘመናዊ ቤቶች ግንባታ አስፈላጊው ቅድመ ዝግጅት መጠናቀቁን አስታውቋል።


 

በዚህም መሠረት፤ የሕንጻ ግንባታ ሳይቶች መረጣ እና ተያያዥ የቅድመ ዝግጅት ሥራዎች አፈጻጸምም በግዛቱ የኮንስትራክሽን እና ቤቶች ኮርፖሬሽን በቀረበ የጥናት ሪፖርት አማካኝነት በዝርዝር ተገምግሟል።

ቀደም ሲል በአዲስ አበባ የተፈረመውን የመግባቢያ ስምምነት ወደ ተግባር የሚያስገባው ይኸው አዲስ ውልም በጁባ ከተማ መፈረሙን ኮርፖሬሽኑ ለኢዜአ የላከው መረጃ አመላክቷል።

ስምምነቱን የፈረሙትም፤የፌዴራል ቤቶች ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈጻሚ ረሻድ ከማል (ዶ/ር) እና የደቡብ ሱዳን ሴንትራል ኢኳቶሪያል ግዛት አሥተዳዳሪ ኢማኑኤል አድል ናቸው።

በዚህም መሠረት ኮርፖሬሽኑ በጁባ ከተማ ዘመናዊ የንግድና የመኖሪያ ሕንጻዎችን የሚገነባ ይሆናል።


 

ከዚሁ ጋር ተያይዞ የኮርፖሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ረሻድ ከማል (ዶ/ር) ከደቡብ ሱዳን መንግሥት ልዩ መልዕክተኛ አዱት ኪር ጋር ውጤታማ ውይይት አድርገዋል።

ዋና ሥራ አስፈጻሚው በዚሁ ወቅት፤ የፌዴራል ቤቶች ኮርፖሬሽን በደቡብ ሱዳን የቤት ልማት ዘርፍ የተሰማራው የጋራ ተጠቃሚነትን፣ አብሮነትን እና ወንድማማችነትን መርኅ አድርጎ መሆኑን አስገንዝበዋል።

በአጭር ጊዜ ውስጥ ሙሉ በሙሉ የቅድመ ዝግጅት ሥራዎችን አጠናቆ ግንባታውን በይፋ እንደሚጀምርም አረጋግጠዋል።

አዱት ኪር በበኩላቸው፥ ኮርፖሬሽኑ በጁባ ከተማ ለሚያካሂደው የቤት ልማት ፕሮግራም የደቡብ ሱዳን የፌዴራል መንግሥት አስፈላጊውን ድጋፍ ሁሉ እንደሚያደርግ ተናግረዋል።

ይህ የቤት ግንባታ መጀመር በሁለቱ እህትማማች ሀገራት መካከል ያለውን ጠንካራና ታሪካዊ ግንኙነት ወደ ላቀ ደረጃ እንደሚያሸጋግረው ያላቸውን ሙሉ እምነትም ገልጸዋል።

የደቡብ ሱዳን መንግሥትም ለስምምነቱ ተግባራዊነት ያለውን ቁርጠኝነት አረጋግጠዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም