ቀጥታ፡

በአዲስ አበባ ከታቀደው በላይ ዜጎች የአምስት ሚሊዮን ኮደርስ ስልጠናን ለመውሰድ ተመዝግበዋል

አዲስ አበባ፤ሰኔ 9/2018(ኢዜአ)፦በአዲስ አበባ በእቅድ ከተያዘው በላይ ዜጎች የአምስት ሚሊዮን ኮደርስ ስልጠናን ለመውሰድ መመዝገባቸውን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ልማት ቢሮ አስታወቀ።

በከተማዋ ከ809 ሺህ በላይ ዜጎች የአምስት ሚሊዮን ኮደርስ ስልጠናን እንዲወስዱ ለማድረግ ታቅዶ፥ ከ996 ሺህ በላይ ዜጎች ስልጠናውን ለመውሰድ መመዝገባቸውን ቢሮው ገልጿል።

እስካሁን ባለው ሂደት ስልጠናውን ለመውሰድ ከተመዘገቡት ዜጎች መካከል ከ742 ሺህ የሚሆኑትም ስልጠናውን በማጠናቀቅ የምስክር ወረቀት ወስደዋል።

ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ የዲጂታል ምህዳር ውስጥ ንቁ ተሳታፊና ተወዳዳሪ ለመሆን በዲጂታል መሠረተ ልማትና በዲጂታል ክህሎት እየተዘጋጀች ነው።

የዚህ ብሔራዊ ግብ አካል የሆነው የአምስት ሚሊዮን ኮደርስ መርሃ ግብር ሐምሌ 16 ቀን 2016 ዓ.ም በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በይፋ መጀመሩ ይታወሳል።

በሦስት ዓመት ውስጥ በሀገር አቀፍ ደረጃ 5 ሚሊዮን ወጣቶች በኦንላይን የኮዲንግ ስልጠና እንዲወስዱ ዓላማ ያነገበ ነው።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በቅርቡ ባስተላለፉት መልዕክት በመርሃ ግብሩ ‎በሦስት ዓመታት ውስጥ ለማሳካት የታቀደውን ግብ ከሁለት ዓመት ባነሰ ጊዜ ውስጥ ማሳካት ተችሏል ብለዋል።

በመርሃ ግብሩ ከ5 ሚሊዮን በላይ ሰልጣኞች ተመዝግበው ከ3 ሚሊዮን በላይ የሚሆኑት ስልጠናውን ማጠናቀቃቸውንና ይህ ስኬት የሕዝቡ ቁርጠኝነት እና ወሰን የሌለው አቅም ማረጋገጫ መሆኑን ተናግረዋል።

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ልማት ቢሮ ምክትል ኃላፊ እና የስማርት ሲቲ ዘርፍ ኃላፊ ዶክተር ቱሉ ጥላሁን ለኢዜአ እንዳሉት፥ የ5 ሚሊዮን ኮደሮች መርሃ ግብር የዲጂታል ክህሎትን የሚያሳድግ ነው።

የኮደርስ ስልጠናዎች የዲጂታል ክህሎትን ከማሳደጋቸው በተጨማሪ የፈጠራ ሃሳብን የሚያጎለብቱና ቴክኖሎጂ ለማልማት የሚችሉበት እድል የሚፈጥር መሆኑንም ተናግረዋል።

በአዲስ አበባ ከ800 ሺህ በላይ የሰው ኃይልን ለማሰልጠን መታቀዱንና ጠቅሰው፥እስካሁን ባለው መረጃ ከ90 በመቶ በላይ ያህል ዜጎች ስልጠናቸውን ማጠናቀቃቸውን ገልፀዋል።

በከተማዋ የአምስት ሚሊዮን ኮደርስ እቅድን ለማሳካት ቢሮው ከባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት እየተሠራ መሆኑንም አንስተዋል።

ቢሮው የዜጎችን የዲጂታል ክህሎት የሚያጠናክሩ ሌሎች ዘመናዊ ስርዓቶችን ወደተግባር በማስገባት ስልጠና ለመስጠት ማቀዱን ተናግረዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) እስከ ነሐሴ 2018 ዓ.ም ድረስ የኮደርስ ሰልጣኞችን ቁጥር 7 ሚሊዮን ለማድረስ መታቀዱንና ይህንን ብሔራዊ ተልዕኮ ለማሳካትም ዜጎች በንቃት እንዲሳተፉ ጥሪ አቅርበዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም