ቀጥታ፡

መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ቀልጣፋ አሰራር ቀደም ሲል የነበረውን ውጣ ውረድ ያስቀረ ነው-ተገልጋዮች

ባህር ዳር፤ሰኔ 7/2018 (ኢዜአ)፦ የባህር ዳር መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ቀልጣፋ አሰራር ቀደም ሲል የነበረውን ውጣ ውረድ ያስቀረ ነው ሲሉ በከተማዋ የአገልግሎት አሰጣጡ ተጠቃሚዎች ገለጹ።

መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ተደራሽነት በመንግስት ተቋማት የሚስተዋሉ የመልካም አስተዳደር ችግሮችን መፍታት ማስቻሉንም ጠቅሰዋል።

ተገልጋዮቹ ለኢዜአ በሰጡት አስተያየት አገልግሎቱ የመንግስት ተቋማትን የመረጃ አያያዝ በማዘመን ቀልጣፋ አሰራርን ገቢራዊ በማድረግ ብልሹ አሰራር ማስቀረቱን ገልጸዋል።


 

አስተያየታቸውን ከሰጡ የባህር ዳር ከተማ ባለጉዳዮች መካከል አቶ ተቀባ ሙሉጌታ እንዳሉት፤ መሶብ የአንድ ማዕከል  አገልግሎት ቀልጣፋ አሰራር  ቀደም ሲል የነበረውን ውጣ ውረድ ያስቀረ ነው።

የንብረት ስም ዝውውር አገልግሎት ለማግኘት መጥተው ጉዳያቸውን በ15 ደቂቃ ውስጥ በተሟላ ሁኔታ ለማጠናቀቅ መቻላቸውን ገልፀዋል። 

አሰራሩ ቀደም ሲል አንድን ጉዳይ ለማስፈጸም ወደተለያዩ ተቋማት በመመላለስ የሚፈጠርን እንግልትና የጊዜ መባከን ለማስቀረት መቻሉን አስረድተዋል።


 

በቴክኖሎጂ የተደራጀው መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ከዚህ ቀደም ሁለትና ሦስት ወራት ይፈጅ የነበረውን ጉዳይ በደቂቃዎች በመጨረስ ፈጣን ምላሽን እየሰጠ ነው ያሉት ደግሞ ሌላው ተገልጋይ አቶ መንግስቴ ጌጡ ናቸው።

አገልግሎት አሰጣጡ የህዝብን እርካታ ያረጋገጠ በመሆኑ የመጡበትን የመንጃ ፈቃድ እድሳት አገልግሎት በፍጥነትና ተገቢ ሁኔታ ማግኘታቸውን ተናግረዋል።

አገልግሎቱን ከብልሹ አሰራር በጸዳና  በአጠረ ጊዜ  በማግኘታቸው መደሰታቸውን ገልጸዋል።


 

ሌላዋ ተገልጋይ ወይዘሮ ፍሬህይወት ወርቁ በበኩላቸው የማዕከሉ ዘመናዊ የደንበኞች አገልግሎት ይበልጥ ሊስፋፋ እንደሚገባ አመልክተዋል። 

የባህር ዳር ከተማ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት አስተባባሪ አቶ ማስረሻ ፈንታ በበኩላቸው፤ አስተዳደሩ የህዝብ አቤቱታ የሚበዛባቸውን 87 አገልግሎቶች በ13 ተቋማት በማደራጀት የተገልጋይን ፍላጎት ለማሟላት መሰራቱን አስረድተዋል።


 

ማእከሉ ወደ ስራ ከገባ በኋላም የተገልጋዮች እርካታን ለማሳደግና ብልሹ አሰራርን ለማስወገድ እንደቻለ ጠቁመው ይህም  ባለፉት ወራት ከ58 ሺህ በላይ ደንበኞችን ማገልገሉን ጠቅሰዋል።

የአገልግሎት አሰጣጡን በየጊዜው በማጥናት አሰራሩን በቴክኖሎጂ የታገዘና ቀልጣፋ በማድረግም የህዝብን እርካታ ከ98 በመቶ  በላይ ማድረስ መቻሉን አብራርተዋል።

በማዕከሉ ከሚሰጠው አገልግሎት በተጨማሪም በኦን ላይን አገልግሎት መስጠት መጀመሩንም አንስተው፤ ይህም የበለጠ ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አረጋግጠዋል።

 

 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም