ቀጥታ፡

'’ብቃት'’ የወጣቶች የሥራ ላይ ልምምድ በክህሎት የተቀረጹ፣ ተወዳደሪና በስራ ዓለም ብቁ የሆኑ ወጣቶችን ማፍራት ያስችላል

አዲስ አበባ፤ ሰኔ 6/2018(ኢዜአ)፦ '’ብቃት'’ የወጣቶች የሥራ ላይ ልምምድ ፕሮግራም በክህሎት የተቀረጹ፣ ተወዳደሪና በስራ ዓለም ብቁ የሆኑ ወጣቶችን ማፍራት እንደሚያስችል የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ ሰሎሞን ሶካ ገለጹ፡፡

ፕሮግራሙ ከዚህ ቀደም በ11 ከተሞች ተግባራዊ ሲደረግ የቆየ ሲሆን ዛሬ ይፋ በሆነው ፕሮግራም 16 ተጨማሪ ከተሞች የተካተቱ ሲሆን በዚህም ከ100 ሺህ በላይ ዜጎች ተጠቃሚ እንደሚሆኑ ተጠቁሟል፡፡

ለሁለት ዓመት የሚቆየው ይህ መርሐ ግብር የወጣቶችን የሥራ አጥነት ችግር በዘላቂነት ለመቅረፍና ስትራቴጂያዊ ትብብሩን ይበልጥ ለማጠናከር ትልቅ ሚና እንደሚጫወት ተመልክቷል።

የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ ሰሎሞን ሶካ በመድረኩ እንደገለጹት፤ መንግሥት የዜጎችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚነት በተሟላ መንገድ ለማረጋገጥ በርካታ ተግባራትን እያከናወነ ይገኛል።


 

በተለይ ከለውጡ ወዲህ በርካታ ዜጎች በተለያየ የሥራ መስክ ተሰማርተው ከራሳቸው አልፈው ቤተሰቦቻቸውን በማገዝ ላይ እንደሚገኙ ጠቅሰዋል፡፡

በተለይም የወጣቶችን የሥራ ዕድል አማራጭ ለማስፋት በመደበኛነት ከሚከናወኑ ተግባራት በተጨማሪ፣ ከዓለም ባንክ ጋር በመተባበር "ብቃት" የተሰኘውን የሥራ ላይ ልምምድ ፕሮግራም ተግባራዊ እያደረገ እንደሚገኝ አንስተዋል።

ይህ ፕሮግራም በከተሞች የሚኖሩ ወጣቶችን በተለያዩ ተቋማት በማሰማራት የሥራ ላይ ልምምድ እንዲያደርጉ የሚያስችል መሆኑን ጠቅሰው፤ ወጣቶቹ በቆይታቸው ከሚያገኙት የተግባር ዕውቀት ባሻገር የሥራ ልምድ እንዲያገኙና በቀላሉ ወደ ሥራ እንዲገቡ የሚያግዝ መሆኑንም ተናግረዋል።

ይህ የሥራ ላይ ልምምድ መርሃ ግብር በቀጣይ በሚከናወነው የማስፋፊያ ሥራ ዕድሜያቸው ከ18 እስከ 29 የሆኑ፣ 12ኛ ክፍልና ከዚያ በታች የሆኑ ሴቶችንና ወጣቶችን ይበልጥ ተጠቃሚ እንደሚያደርግም ገልጸዋል፡፡

ወደ ፕሮግራሙ የምትገቡ አዳዲስ ከተሞች ከነባር ከተሞች የተገኙ መልካም ተሞክሮዎችን በመቅሰም ለላቀ ውጤት መዘጋጀት አለባችሁ ሲሉም ሚኒስትር ዴኤታው አስገንዝበዋል፡፡


 

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ሥራና ክህሎት ቢሮ ምክትል ቢሮ ኃላፊ አስፋው ለገሰ፤ ''ብቃት'' የተሰኘው የሥራ ላይ ልምምድ ፕሮግራም የስድስት ወር የሥራ ላይ ሥልጠና ቆይታ እንዳለው ተናግረዋል፡፡

ፕሮግራሙ የከተማዋ ወጣቶች በመረጡት ዘርፍ ሥልጥነው ወደ ሥራ እንዲሰማሩ ትልቅ አቅም መሆኑንም ተናግረዋል፡፡


 

የአማራ ክልል ሥራና ክህሎት ቢሮ ምክትል ቢሮ ኃላፊ አወቀ ዘመነ በበኩላቸው፤ "ብቃት" የተሰኘው የሥራ ላይ ልምምድ ፕሮግራም በክልሉ ሰባት ከተሞች ተግባራዊ እየተደረገ እንደሚገኝ አመላክተዋል፡፡

ፕሮግራሙ በክልሉ 12ኛ ክፍል እና ከዚያ በታች የትምህርት ዝግጅት ያላቸውን ወጣቶች ተጠቃሚ ለማድረግ ጉልህ ሚና እያበረከተ ይገኛል ብለዋል፡፡

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም