ቀጥታ፡

መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት እንግልትንና አላስፈላጊ ወጪን በማስቀረት፣ ቀልጣፋ አገልግሎት እንድናገኝ አስችሎናል

አዲስ አበባ፤ ሰኔ 6/2018(ኢዜአ)፦ የአዲስ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ስራ መጀመሩ እንግልትንና አላስፈላጊ ወጪን በማስቀረት ፈጣንና ቀልጣፋ አገልግሎት እንድናገኝ አስችሎናል ሲሉ ተገልጋዮች ገለጹ።

ዜጎች በመንግስት አገልግሎት አሰጣጥ ላይ የሚገጥማቸውን እንግልትና ቅሬታ ለመፍታት በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሀሳብ አመንጪነት ወደ ሥራ የገባው መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት መንግስት ለዜጎች የሚሰጠውን አገልግሎት በማላቅ ላይ ይገኛል፡፡

አዲስ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ተደራሽነቱን በማስፋት በመንግሥት አገልግሎት ጥራትን በማረጋገጥ የተገልጋዮችን እርካታ እያሳደገ ይገኛል፡፡

ኢዜአ በመዲናዋ አገልግሎት መስጠት ላይ ከሚገኙት ማዕከላት መካከል በአዲስ ከተማ እና በቂርቆስ ክፍለ ከተሞች የሚገኙ የ"አዲስ መሶብ" ቅርንጫፎችን የአገልግሎት አሰጣጥ በመቃኘት ተገልጋዮችን አነጋግሯል፡፡


 

በማዕከሉ ያነጋገርናቸው አካል ጉዳተኛዋ ወይዘሮ ዘነበች አለኝታ፤ ከዚህ ቀደም አገልግሎት ለማግኘት ወደ ቢሮ መመላለስ በራሱ ትልቅ ፈተና እንደነበር ገልጸዋል።

ዛሬ ወደ ማዕከሉ ከገቡበት ሰዓት ጀምሮ ጉዳያቸውን ጨርሰው እስከሚወጡ ድረስ ያለው ሂደት እጅግ የተቀላጠፈ መሆኑንና

በተለይም ለአካል ጉዳተኞችና ለአቅመ ደካሞች ልዩ ትኩረትና ቅድሚያ መስጠቱ ቀደም ሲል ይገጥማቸው የነበረውን እንግልት መቅረፉን ተናግረዋል።


 

የቂርቆስ ክፍለ ከተማ የአንድ ማዕከል ተገልጋይ ኢንስፔክተር የኔነሽ መርጋ የማዕከሉ በቴክኖሎጂ የተደገፈ አሰራር ግልጽነትን በመፍጠር መጉላላትን ማስቀረቱን ገልጸዋል።


 

በተመሳሳይ አቶ መኳንንት ይንገስ እና ወይዘሮ ዳቤልቱ ቲቻ የሰራተኞቹ መልካም መስተንግዶና ቅልጥፍና አገልግሎቱን በፍጥነት አግኝተው ያለምንም መስተጓጎል ወደ እለት ተእለት ስራቸው እንዲመለሱ በእጅጉ እንደረዳቸው ጠቁመዋል።


 

የአገልግሎቱን አሰጣጥ በተመለከተ በቂርቆስ ክፍለ ከተማ የሲቪል ምዝገባና የነዋሪዎች አገልግሎት ሰጪ ባለሙያ የሆኑት ይስሀቅ ተስፋዬ፤ ተገልጋዮች የተለያዩ አገልግሎቶችን በአንድ ቦታ ማግኘት መቻላቸው እንግልት ማስቀረቱን ተናግረዋል፡፡


 

የአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ የአንድ ማዕከል ባለሙያዋ አቢጊያ ቁምላቸው፤ በማዕከሉ ያሉ አገልግሎቶች በሙሉ ዲጂታላይዝድ መደረጋቸውን ገልጻ ይህም ቀደም ሲል በወረቀት አሰራር ወቅት የነበረውን የፋይል መጥፋትና መዘግየት ችግር ሙሉ በሙሉ በመፍታት፣ አስተማማኝና ደህንነቱ የተጠበቀ አሰራር መዘርጋቱን አብራርታለች።


 

የአዲስ መሶብ የአንድ ማዕከል ዲጂታል አገልግሎት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ቴድሮስ ማስረሻ፤ ተቋማቸው ፈጣንና ቀልጣፋ አሰራርን በማስፈን የህዝቡን እርካታ ይበልጥ ለማሳደግ በቁርጠኝነት እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል።

በተለይም ከፍተኛ የህዝብ ፍላጎት ባለባቸው የአገልግሎት ዘርፎች ላይ ትኩረት በማድረግ፣ የአገልግሎት ጥራትንና ተደራሽነትን በየጊዜው እያሻሻሉ እንደሚገኙ አብራርተዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም