በቆላማ አካባቢዎች የአየር ንብረት ለውጥን መቋቋም የሚያስችሉ ውጤታማ የውሃና መስኖ ፕሮጀክቶች ዕውን እየሆኑ ነው - ኢዜአ አማርኛ
በቆላማ አካባቢዎች የአየር ንብረት ለውጥን መቋቋም የሚያስችሉ ውጤታማ የውሃና መስኖ ፕሮጀክቶች ዕውን እየሆኑ ነው
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 6/2018 (ኢዜአ)፦ በቆላማ አካባቢዎች የአየር ንብረት ለውጥን መቋቋም የሚያስችሉ ውጤታማ የውሃና መስኖ ፕሮጀክቶች ዕውን እየሆኑ እንደሚገኝ የመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስቴር ገለጸ።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በቅርቡ በቦረና ዞን ባደረጉት ጉብኝት እንዳሉት፤ እንደ ቦረና ባሉ ቆላማ አካባቢዎች የተገነቡ የመስኖ ፕሮጀክቶች የአየር ንብረት ለውጥን በመቋቋም የውሃ መሠረተ ልማትን ለማረጋገጥ ትልቅ ምዕራፍ ከፍቷል፡፡
በኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን መቋቋም የሚያስችሉ አነስተኛ፣ መካከለኛና ከፍተኛ የውሃና መስኖ መሰረተ ልማት እየተገነቡ ይገኛል።
በመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስቴር የቆላማ አካባቢ ኑሮ ማሻሻያ ፕሮጀክት አስተባባሪ ሰይድ ዑመር ለኢዜአ እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ የድርቅ ተፅዕኖን መቋቋም የሚያስችል አቅም እየፈጠረች ነው።
በሀገር አቀፍ ደረጃም የአርሶና አርብቶ አደሩን የድርቅ ተጋላጭነት ለመቀነስ በሁለት ምዕራፍ የተቀረጹ የኑሮ ማሻሻያ ስትራቴጂክ ፕሮጀክቶች እየተገነቡ መሆኑን ገልጸዋል።
ይህም የአርሶና አርብቶ አደሩን የአየር ንብረት ለውጥ የድርቅ ተጋላጭነት የሚቀነስ የውሃና መስኖ የልማት ፕሮጀክቶች ዕውን እንዲሆኑ እያደረገ ነው ብለዋል።
በመጀመርያ ምዕራፍም በሰባት ክልሎች በሚገኙ መቶ ወረዳዎች የውሃ፣ መስኖ፣ መኖና አማራጭ ገቢ ማስገኛ ፕሮጀክቶችን በመገንባት 2 ነጠብ 9 ሚሊየን ዜጎች ተጠቃሚ መደረጋቸውን ተናገረዋል።
የተጠናቀቁት 218 ስትራቴጂክ ፕሮጀክቶችም አንድ መቶ ሥድስቱ የውሃ፤ አስራ አንዱ ደግሞ ከ2 ሺህ ሔክታር መሬት በላይ ማልማት የሚያስችሉ የመስኖ ፕሮጀክቶች መሆናቸውን አስታውቀዋል።
በእንስሳት ሃብት ላይ የሚደርሰውን ተፅዕኖ ለመቀነስም ከ217 ሺህ ቶን በላይ መኖ ማልማት የሚያስችሉ ፕሮጀክቶች እውን መሆናቸውን አንስተዋል።
በሁለተኛው ምዕራፍም ከልማት አጋሮች የተገኘን 424 ሚሊየን ዶላር የገንዘብ ድጋፍ ድርቅና ድንገተኛ አደጋን ምላሽ የሚሰጡ ፕሮጀክቶችን ለመገንባት ወደ ተግባር ተገብቷል ብለዋል።
በ2018 ዓ.ም በጀት ዓመት በስምንት ክልሎች በሚገኙ 120 ወረዳዎች የድርቅና ድንገተኛ አደጋ ምላሽ ሰጪ የውሃና መስኖ ፕሮጀክቶች በግንባታ ላይ እና ለግንባታ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል።
በተጨማሪም በሀገር አቀፍ ደረጃ በአማራጭ ገቢ ማስገኛ ፕሮጀክቶች በርካታ ወጣቶች ተደራጅተው ተጠቃሚ እንዲሁኑ እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል።