ኢትዮጵያ የአስደናቂ ባህል፣ ታሪክና ቅርስ ባለቤት ሀገር መሆኗን በጉብኝታችን አረጋግጠናል - ኢዜአ አማርኛ
ኢትዮጵያ የአስደናቂ ባህል፣ ታሪክና ቅርስ ባለቤት ሀገር መሆኗን በጉብኝታችን አረጋግጠናል
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 6/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የአስደናቂ ባህል፣ ታሪክና ቅርስ ባለቤት ሀገር መሆኗን በጉብኝታቸው ማረጋገጣቸውን በአዲስ አበባ የሚገኙ የዲፕሎማቲክ እግር ኳስ ቡድን አባላት ገለጹ፡፡
የመዲናዋን ገጽታና የቱሪዝም መዳረሻዎቿን ለዓለም በማስተዋወቅ ስፖርት ያለው ሚና የላቀ መሆኑን የአዲስ አበባ ከተማ ቱሪዝም ኮሚሽን አስታውቋል፡፡
የ2026ቱ የዓለም ዋንጫ መጀመሩን ምክንያት በማድረግ በአዲስ አበባ የሚገኙ የተለያዩ ሀገራት ኤምባሲዎችና ዓለም አቀፍ ተቋማት የተሳተፉበት የዲፕሎማቲክ እግር ኳስ ውድድር ተዘጋጅቷል።
በውድድሩ የሚሳተፉ የዲፕሎማቲክ እግር ኳስ ቡድን አባላት እንዲሁም የውድድሩን ዋንጫ አዘጋጅተው ያመጡ የሀገራት እንግዶች በከተማዋ የሚገኙ ዋና ዋና የቱሪስት መስህቦችን ጎብኝተዋል፡፡
እንግዶቹ በኢትዮጵያ ብሔራዊ ሙዚየም፣ በዓድዋ ድል መታሰቢያ እና በአዲስ ስፖርት ፓርክ ባደረጉት ቆይታ የሀገሪቱን እምቅ ባህል፣ ታሪክና ቅርሶች መመልከታቸውን ገልጸዋል፡፡
በጉብኝቱ ወቅት አስተያየታቸውን የሰጡን ከእንግሊዝ የመጡት ማርክ ሃዬስ ጉብኝቱ ስለ ኢትዮጵያ ብዙ አዳዲስ ነገሮችን እንዲያውቁ እንደረዳቸው ተናግረዋል፡፡
ከእንግሊዝ እግር ኳስ ማህበር ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ኢትዮጵያ የመጡት ጎርዶን ጆንሶን በበኩላቸው በኢትዮጵያ በተመለከቱት የህዝብ ለህዘብ ትስስር፣ መስተጋብር፣ መከባበርና የእንግዳ አቀባበል ባህል መደነቃቸውን ገልጸዋል።
በብሔራዊ ሙዚየም የተመለከቱት ቅርስ ኢትዮጵያ ጥንታዊት ሀገር ብቻ ሳትሆን የሰው ዘር መገኛነቷን ያረጋገጡበት መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡
በአዲስ አበባ በሚገኘው የተባበሩት መንግስታት የምግብና ግብርና ተቋም ሠራተኛ የሆነው ኡጋንዳውው ጆሴፍ ኪሩሌ፤ ከጉብኝቱ ኢትዮጵያ ታሪክ፣ የሰው ዘር መገኛነትና ወራሪ ኃይልን ድል ስላደረገችበት የአሸናፊነት ታሪክ ጠቃሚ እውቀት ማግኘታቸውን ገልጸዋል፡፡
ኢትዮጵያ የቀኝ ገዥዎችን ምኞት ያከሸፈች አኩሪ ታሪክ ያላትና በአሁኑ ወቅትም በከፍተኛ የዕድገት ጎዳና ላይ የምትገኝ ሀገር መሆኗን መታዘቡን የገለፀው ከካሜሮን የመጣው ሎይስ ኮቫሞ ነው።
የአዲስ አበባ ከተማ ቱሪዝም ኮሚሽን የዲጂታል ማርኬቲንግና ፕሮሞሽን ዳይሬክተር ፍሬሕይወት ገብረመድን በዚህ ወቅት እንደገለጹት፤ አዲስ አበባ ዓለም አቀፍና አህጉራዊ ኹነቶች በድምቀት እያስተናገደች ትገኛለች ብለዋል።
በዚህም ለተለያዩ ስብሰባዎችና ኮንፍረንሶች ወደ መዲናዋ ለሚመጡ እንግዶች የከተማዋን ገጽታና ሰው ሰራሽ እንዲሁም ታሪካዊ መስህቦች ማስተዋወቅ ለሀገሪቱ ሁለንተናዊ ዕድገት ወሳኝ መሆኑን አስገንዝበዋል፡፡
ስፖርት ቱሪዝም ንቁና ጠንካራ ዜጋ ከመፍጠር ባለፈ፣ የተለያዩ የማህበረሰብ ክፍሎችን በማገናኘት የህዝብ ለህዘብ ትስስርን እንደሚያጠናክርና የመዲናዋን ገጽታ ለዓለም ለማስተዋወቅ የላቀ ሚና እንዳለው አብራርተዋል፡፡
ኮሚሽኑ ይህንን ታሳቢ በማድረግ ያዘጋጀው የዲፕሎማቲክ እግር ኳስ ውድድርና የጉብኝት መርሃ ግብርም የዚሁ ታላቅ ዓላማ አካል መሆኑን አስታውቀዋል፡፡