ቀጥታ፡

የጂንካ ከተማ ዲጂታላይዝድ ማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎት ተገልጋዮች በአጭር ጊዜ ውስጥ ጉዳያቸውን እንዲፈጽሙ አስችሏል

ጂንካ፤ ሰኔ 5 /2018 (ኢዜአ)፦የጂንካ ከተማ ዲጂታላይዝድ ማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎት ተገልጋዮች በአጭር ጊዜ ውስጥ ጉዳያቸውን እንዲፈጽሙ ማስቻሉ ተገለጸ፡፡

የከተማው የአንድ ማዕከል ማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎት በከተማዋ ቀደም ሲል በአሰራር ሲስተዋል የነበረውን ችግር በመፍታት የተገልጋዮችን እንግልት ማስቀረቱን ባለጉዳዮች ተናግረዋል።

የአገልግሎት አሰጣጡን አስመልክቶ ኢዜአ ካነጋገራቸው ተገልጋዮች መካከል አቶ ስሜነህ ካሳሁን እንደገለፁት፤ የማዘጋጃ ቤቱ  የቀደመ አሰራር ኋላ ቀር በመሆኑ ተገልጋዩን ለውጣ ውረድ ሲያጋልጥ ቆይቷል።

ይህን ችግር ለመፍታት በአሁኑ ወቅት የተጀመረው የአንድ ማዕከል ማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎት በዲጂታል ታግዞ መሰጠቱ በአጭር  ጊዜ ውስጥ ጉዳያቸውን ለመፈጸም እንዳስቻላቸው ተናግረዋል።

ሌላኛው የማዘጋጃ ቤቱ ተገልጋይ አቶ አሊ ሙሐመድ በበኩላቸው፤ በአንድ ማዕከል ማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎት የታዩ የአሰራር ለውጦችን ወደ ሌሎች ተቋማት ማስፋት እንደሚገባ ተናግረዋል።

አገልግሎቱ ከቢሮክራሲና ሙስና የፀዳ መሆኑ ቀደም ሲል በአገልግሎት አሰጣጥ ይስተዋል የነበረን የመልካም አስተዳደር ችግር መፍታቱንም አመልክተዋል።

የጂንካ ከተማ አስተዳደር ማዘጋጃ ቤት የአንድ ማዕከል አስተባባሪ አቶ ተመስገን ጋናቡል በበኩላቸው፤ የማዘጋጃ ቤቱን አሰራር ለማዘመን ለሰው ሀይል ልማትና ለቴክኖሎጂ ትኩረት ተሰጥቷል ብለዋል።

ማዘጋጃ ቤቱ ቀደም ሲል በወረቀት አገልግሎቶችን ሲሰጥ በነበረባቸው ወቅቶች ፋይል ከመጥፋት ባለፈ በተገቢው ባለመደራጀት ለፍለጋ ሲወስድ የነበረን ረጅም ጊዜ ለማስቀረት ወደ ዲጂታል የምዝገባ ስርአት መግባቱን ጠቁመዋል። 

በዲጂታል ቴክኖሎጂው የአንድ ተገልጋይ ጉዳይ ምን ያህል ጊዜ እንደፈጀ መተግበሪያው መረጃ መስጠቱ  የተጠያቂነት አሰራርን በመዘርጋት ብልሹ አሰራርን  ለማስወገድ ማስቻሉን ገልጸዋል።

በአሁኑ ወቅት በማዘጋጃ ቤቱ ዲጂታል አገልግሎት የስም ዝውውር ለማድረግ፣ የይዞታ ማረጋገጫ ሰርተፍኬት ለማግኘት፣ የግንባታ ፈቃድ ለመውሰድ፣ ለዋስትና አገልግሎቶች እና ለማንኛውም ከመሬት ጋር ተያይዞ ለሚቀርቡ ጥያቄዎች ፈጣን ምላሽ እየተሰጠ ነው ብለዋል።

በቀጣይም እንደ ባንክ፣ ፖስታ ቤት፣ ቴሌኮም፣ ኤሌክትሪክና እና ውሃ ያሉ አገልግሎቶችን ከማዕከሉ ጋር በማስተሳሰር ተገልጋዮች በአንድ ማዕከል ዘርፈ-ብዙ አገልግሎት የሚያገኙበት ሁኔታም እንደሚመቻች አስተባባሪው አስታውቀዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም