ቀጥታ፡

መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ብልሹ አሰራሮችን በማስቀረት ቀልጣፋ አገልግሎት እየሰጠ ነው

አሶሳ፤ ሰኔ 5 /2018 (ኢዜአ)፦ የአሶሳ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ቀደም ሲል የነበሩ የአሰራር ግድፈቶችን በማስቀረት፣ ቀልጣፋ አገልግሎት እየሰጠ መሆኑን ተገልጋዮች ገለጹ።

የአገልግሎት አሰጣጥ ችግሮችን ለመቅረፍ እና ሁሉንም አገልግሎቶች በአንድ ጣራ ስር ተደራሽ ለማድረግ የአሶሳ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት የአስተዳደሩን አራት ተቋማትና ከፌዴራል ሶስት ተቋማትን ይዞ ባለፈው መጋቢት ወር በ38 አገልግሎቶች ስራ መጀመሩ ይታወሳል።

ይህ አዲስ አሰራር ደንበኞች ያለምንም እንግልትና ተጨማሪ ወጪ ፈጣን ምላሽ እንዲያገኙ በር የከፈተ ሲሆን፣ የአሁኑ የተገልጋዮች ምስክርነትም ተቋሙ ያስመዘገበውን ውጤታማነት በተጨባጭ የሚያሳይ ነው።

በአሶሳ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት የንብረት ውክልና ለመስጠት የመጣው ሰኢድ ጁሃር እና የንግድ ፈቃድ ለማውጣት የመጣችው ወጣት ጁፒተር አወል፤ በማዕከሉ ሁሉንም አገልግሎት በአንድ ቦታ አግኝተናል ብለዋል።

አገልግሎቱ ፈጣን፣ ግልጽ እና ወጪ ቆጣቢ ከመሆኑም በላይ የተገልጋዮችን ክብር በጠበቀ መልኩ እንዲስተናገዱ በሚያደርግ የህዝቡን የመልካም አስተዳደር እጦት ጥያቄ የመለሰ ማዕከል መሆኑን ገልጸዋል።

ማዕከሉ በቀጣይ ሌሎች የከተማ አስተዳደሩን ተቋማት እንዲያካትትም ተገልጋዮቹ ጠይቀዋል።

በማዕከሉ ያገኘናቸው ተገልጋይ አቶ አብዱ ካሳው በበኩላቸው፤ አገልግሎቱ የጊዜ ቀጠሮን እና መጉላላትን በማስቀረት ለተገልጋዮች እፎይታን የፈጠረ እንደሆነ ገልጸዋል።

የአሶሳ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ዳይሬክተር አቶ ቢራራ ካሳ፤ ማዕከሉ ስራ ከጀመረ በጥቂት ወራት ጊዜ ውስጥ ከ1 ሺህ 600 በላይ ዜጎች የተለያዩ አገልግሎቶችን ማግኘታቸውን ተናግረዋል።


 

ማዕከሉ በቀን ከ 135 በላይ ተገልጋዮችን እያስተናገደ መሆኑን ገልጸው፥ በተለይም የንግድ ፍቃድ ውክልና እና ሌሎች ተያያዥነት ያላቸው አገልግሎት ፈላጊዎች በብዛት እንደሚስተናገዱ ጠቅሰዋል።

በቀጣይም በከተማዋ የመልካም አስተዳደር ችግር የሚታይባቸውን ተቋማት በመለየት አገልግሎታቸውን ወደ ማዕከሉ እንዲያስገቡ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን አስታውቀዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም