ቀጥታ፡

ረቂቅ አዋጁ አነስተኛ ይዞታ ያላቸውን አርሶ አደሮችና አርብቶ አደሮችን ወደ ዘመናዊ፣ ተወዳዳሪ እና ገበያ መር ሥርዓት ለማሸጋገር ጉልህ አስተዋጽኦ ይኖረዋል

አዲስ አበባ፤ሰኔ 3/2018 (ኢዜአ)፦የግብርና ቢዝነስ ኩባንያ ረቂቅ አዋጅ አነስተኛ ይዞታ ያላቸውን አርሶ አደሮች፣ አርብቶ አደሮችና ከፊል አርብቶ አደሮችን ወደ ዘመናዊ፣ ተወዳዳሪ እና ገበያ መር ሥርዓት ለማሸጋገር ጉልህ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው የግብርና ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ገለጸ።

የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የግብርና ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ በግብርና ቢዝነስ ኩባንያ ረቂቅ አዋጅ ላይ የአስረጂ መድረክ አካሂዷል።


 

በኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት የፖለሲና የምግብ ስርዓትና ጥናት ሲኒየር ዳይሬክተር ረታ ዋጋሪ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ አነስተኛ ይዞታ ያላቸውን አምራቾች በኩባንያ በማደራጀት፣ መሬት የመጠቀም መብታቸውን፣ የእንስሳት ሀብታቸውንና ጉልበታቸውን ወደ ካፒታል በመለወጥ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ የሚያስችል ግልጽ የሕግ ማዕቀፍ ባለመኖሩ ረቂቅ አዋጁ መዘጋጀቱን አብራርተዋል።

ረቂቅ አዋጁ በርካታ ዓላማዎች ያካተተ መሆኑን የጠቀሱት ዳይሬክተሩ  ለዘርፉ ዕድገት ምቹ የሆነ ግልጽ አሠራር መዘርጋት፣ አነስተኛ ይዞታ ያላቸው አምራቾች ወደ መካከለኛ አልሚነት በመሻገር ኑሮአቸውን እንዲያሻሽሉ ማስቻል እንዲሁም ለገጠር ትራንስፎርሜሽን እውን መሆን የጎላ አስተዋጽኦ ማድረግ የሚሉ ተጠቃሽ ናቸው ብለዋል፡፡

አዋጁ ለአነስተኛ ይዞታ አምራቾች የፋይናንስ እና የኢንሹራንስ ተደራሽነትን በማመቻቸት፣ ከዘመናዊ አሠራርና አገልግሎቶች ተጠቃሚ ለማድረግ የሚያስችል መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ 

የግብርና ቢዝነስ ኩባንያዎች የማቋቋሚያ ካፒታል፣ የአባላት ምዝገባ ፣ የኩባንያዎች አደረጃጀት ፣ የተቋማት ስልጣንና ተግባር የሕግ ተጠያቂነትና ሌሎች ጥያቄዎች ከቋሚ ኮሚቴው አባላት ተነስተዋል።   

በግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት አማካሪ አቶ ሽመክት ማሩ በሰጡት ማብራሪያ፤ በረቂቅ አዋጁ ላይ የተቀመጡት የኩባንያዎች መሥራች አባላት ቁጥር እና የማቋቋሚያ መነሻ ካፒታል መስፈርቶች መካተታቸውን ጠቅሰዋል፡፡

መስፈርቶቹ ባለፉት ዓመታት በሀገሪቱ የግብርና ዘርፍ ከተገኙ ልምዶች፣ ከዓለም አቀፍ ተሞክሮዎችና ጥልቅ ጥናቶች ላይ ተመስርተው የተቀረጹ መሆናቸውን አስገንዝበዋል።

የኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ማንደፍሮ ንጉሤ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ረቂቅ አዋጁ የተዘጋጀበት ዋና ዓላማ የግብርና ግብዓትና ቴክኖሎጂ አቅርቦትን በማሳለጥና ተደራሽ በማድረግ የአነስተኛ ይዞታ አምራቾችን ምርት፣ ምርታማነትና ገቢ ለማሳደግ መሆኑን አንስተዋል።

አዋጁ የግብርና ምርትን በከፍተኛ መጠንና ጥራት በማሰባሰብ፣ የግብይትና የእሴት ጭመራ ተግባራትን በማዘመን ረገድ ትልቅ አቅም እንደሚፈጥር ገልጸዋል። 

ይህ መሆኑ የአነስተኛ ይዞታ አምራቾችን የኑሮ ደረጃ ከማሻሻሉም በላይ ለሀገሪቱ አጠቃላይ ኢኮኖሚ ዕድገት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዲያበረክቱ ያሰችላቸዋል ብለዋል።

የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የግብርና ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ሰለሞን ላሌ፤ ረቂቅ አዋጁ አነስተኛ ይዞታ ያላቸውን አርሶ አደሮች፣ አርብቶ አደሮችና ከፊል አርብቶ አደሮችን በግብርና ቢዝነስ ኩባንያ በማደራጀትና በማቀናጀት፣ ምርታማነትን ለማጎልበትና የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ጉልህ ሚና እንዳለው ገልጸዋል፡፡

አዋጁ በግብርናው ዘርፍ የእሴት ጭመራን ለማምጣት እንዲሁም ወደ ውጭ የሚላኩ ምርቶችን በማሳደግ የዜጎችን ተጠቃሚነት ለማጎልበት እንደሚያስችል ጠቅሰዋል።

 

 

 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም