ቀጥታ፡

ተቋሙ አገልግሎት አሰጣጡን ቀልጣፋና ምቹ የሚያደርጉ በርካታ የዲጂታላይዜሽን ስራዎችን እያከናወነ ነው

አዲስ አበባ፤ ሰኔ 3/2018 (ኢዜአ)፦የትምህርት ምዘናና ፈተናዎች አገልግሎት አሰራሩን ዘመናዊ ከማድረግ ባለፈ የአገልግሎት አሰጣጡን ቀልጣፋና ምቹ የሚያደርጉ በርካታ የዲጂታላይዜሽን ስራዎችን እያከናወነ መሆኑን የአገልግሎቱ ዋና ዳይሬክተር እሸቱ ከበደ (ዶ/ር) አስታወቁ፡፡ 

ሀገር አቀፍ ፈተናዎችን በበይነ-መረብ ለተፈታኞች ማድረስ የሚያስችል አቅም መፈጠሩንም አመልክተዋል፡፡

በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት ይፋ የተደረገው የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ በሀገሪቱ የዲጂታላይዜሽን ጉዞ ላይ ከፍተኛ ውጤት ማስመዝገቡ ይታወቃል።

ይህንን ተከትሎ በቅርቡ ይፋ ሆኖ በትግበራ ላይ የሚገኘው የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂም ሀገሪቱን በዲጂታል ዘርፍ ይበልጥ ውጤታማ ለማድረግ ሰፊ አስተዋጽኦ እያበረከተ ይገኛል።

የትምህርት ምዘናና ፈተናዎች አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር እሸቱ ከበደ (ዶ/ር) ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ እንደገለጹት፤ ኢትዮጵያ በዲጂታል ግንባታ ዘርፍ እያከናወነችው ባለው ተግባር ዘርፈ-ብዙ ስኬቶች እየተመዘገቡበት ነው፡፡

ኢትዮጵያ በምታደርገው በዚህ የዲጂታላይዜሽን ጉዞ ተቋማቸው የራሱን ሚና ለመጫወት አሰራሩን በቴክኖሎጂ የመቃኘት ሰፊ ተግባራትን እያከናወነ እንደሚገኝ ገልጸዋል።

በዚህም ተቋሙ የሚሰጣቸውን ልዩ ልዩ አገልግሎቶች ዘመኑን የዋጁ ለማድረግ እየተቻለ መሆኑን አንስተዋል፡፡

በዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ ትግበራ ወቅት የተለያዩ ሀገር አቀፍ ፈተናዎችን በአብዛኛው በበይነ-መረብ ለተፈታኞች ማድረስ የሚያስችል አቅም መፈጠሩን አመልክተዋል።

ከተፈታኞች ባሻገር ሌሎች አገልግሎት ፈላጊዎችም ከተቋሙ ድረ-ገጽና የበይነ-መረብ መተግበሪያዎች ጋር ተያያዥ የሆኑ ምቹ አሰራሮች መዘርጋታቸውን ዳይሬክተሩ ጠቁመዋል።

በዚህም መሠረት ዜጎች በአካል ወደ ተቋሙ መምጣት ሳይጠበቅባቸው ባሉበት ቦታ ሆነው፤ የጠፋባቸውን ወይም የተበላሹባቸውን የትምህርት ማስረጃዎች ማመልከትና ለጥያቄዎቻቸው ምላሽ ማግኘት የሚችሉበት አሰራር መፈጠሩን አብራርተዋል።

በተጨማሪም የትምህርት ማስረጃ ማጣራት ጥያቄዎችም በተመሳሳይ ሁኔታ ሙሉ በሙሉ በዲጂታል መንገድ ምላሽ እንዲያገኙ መደረጉን ገልጸዋል።

ተቋሙ በቀጣይም ከዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ጋር አብሮ ለመራመድና ለዜጎች የሚሰጡ አገልግሎቶችን ይበልጥ ተደራሽ ለማድረግ ቴክኖሎጂን የማላመድና አቅምን የማሳደግ ስራውን አጠናክሮ እንደሚቀጥል ዋና ዳይሬክተሩ አስታውቀዋል።

ይህም ማህበረሰቡ ከዲጂታላይዜሽን ተጠቃሚ እንዲሆንና የተቋሙ አገልግሎት ተደራሽነት ይበልጥ እንዲሰፋ ትልቅ ሚና እንደሚጫወት አመልክተዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም