ቀጥታ፡

የሌማት ትሩፋት ኢኒሼቲቭ በወተት ምርታማነት ላይ ተጨባጭ ውጤት እያስመዘገበ ነው

አዲስ አበባ፤ ሰኔ 1/2018(ኢዜአ)፦ የሌማት ትሩፋት ኢኒሼቲቭ በወተት ምርታማነት ላይ ተጨባጭ ውጤት እያስመዘገበ መሆኑን የግብርና ሚኒስቴር አማካሪ ሚኒስትር ደኤታ ኢፋ ሙለታ (ዶ/ር) ገለጹ።

የኢትዮጵያ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት በባዮ ቴክኖሎጂ ምርምር "ኢቲቱ" የተሰኘ ወተት ማርጋት የሚያስችል የፕሮ ባዮቲክ እርሾ ይፋ አድርጓል።


 

የኢትዮጵያ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት የዓለም የወተት ቀንን አስመልክቶ የጋራ የውይይት መድረክ እና አውደ-ርዕይ አካሂዷል።

የግብርና ሚኒስቴር አማካሪ ሚኒስትር ደኤታ ኢፋ ሙለታ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ "ኢቲቱ" የፕሮ ባዮቲክ እርሾ ከውጭ የሚገባውን ምርት በማስቀረት የውጭ ምንዛሪን ማዳን የሚያስችል ነው፡፡

ይህም በወተት እና የወተት ተዋጽኦ ምርታማነት ላይ ጉልህ አስተዋጽኦ እንዳለው ጠቁመዋል።

በተጨማሪም ኢትዮጵያ በግብርና ፖሊሲ የምግብ ዋስትናንና ስነ-ምግብን ለማጠናከር እያከናወነች ያለውን ስራ የሚያግዝ መሆኑን ተናግረዋል።

በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሀሳብ አመንጪነት የተተገበረው የሌማት ትሩፋት ኢኒሼቲቭ በወተት ምርታማነት ላይ ተጨባጭ ውጤት እያስመዘገበ እንደሚገኝ ተናግረዋል።

ባለሀብቶች በዘርፉ እንዲሰማሩ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከቱን ተናግረው በዛሬው ዕለት ይፋ የተደረገው "ኢቲቱ" የፕሮ ባዮቲክ እርሾ አምራቹን እና የዘርፉን ተዋንያን የሚያነቃቃ መሆኑን ጠቁመዋል።


 

የኢትዮጵያ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ፕሮፌሰር ንጉሴ ደቻሳ በበኩላቸው "ኢቲቱ" የተሰኘው አዲሱ የፕሮ ባዮቲክ እርሾ በሀገሪቱ ያሉ የወተት ማቀነባበሪያ ድርጅቶች በውጭ ምንዛሪ ከውጭ አስገብተው የሚጠቀሙበትን እርሾ የሚተካ ነው ብለዋል።

ይህ የምርምር ውጤት የውጪ ምንዛሪ ወጪን ከማዳን ባለፈ፣ ፓስቸራይዝድ የሆነ ወተትን በአራት ሰዓታት ውስጥ ማርጋት ያስችላል ነው ያሉት።

ኢንስቲትዩቱ ምርምር ከሚያደርግባቸው የግብርና ውጤቶች መካከል ወተትና የወተት ተዋጽኦዎች ዋነኞቹ መሆናቸውን ገልጸው፤ ምርቱ ለምግብ ዋስትና እና ለጤንነት ወሳኝ የሆኑ ንጥረ ነገሮችን የያዘ መሆኑን አብራርተዋል።

ኢንስቲትዩቱ የተሻሻሉ የሰብል እና የእንስሳት ዝርያዎችን በምርምር በማውጣት ለዘርፉ እድገት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ እንደሚገኝም ጠቅሰዋል፡፡

በአሁኑ ወቅትም በወተት ምርታማነት ላይ ትኩረት ያደረጉ በባዮ ቴክኖሎጂ የታገዙ ልዩ ልዩ ምርምሮች እየተከናወኑ እንደሚገኙ አስታውቀዋል።

"ኢቲቱ" የፕሮ ባዮቲክ እርሾ ምርታማነትን በከፍተኛ ሁኔታ እንደሚያረጋግጥ የገለጹት ደግሞ የሰበታ አግሮ ኢንዱስትሪ ዋና ስራ አስፈጻሚ እና የኢትዮጵያ ዴይሪ ማህበር ፕሬዝደንት ሙልጌታ ይመር ናቸው።


 

እንዲሁም የምርት ሂደትን የሚያፋጥንና በሀገር ውስጥ መመረቱ ተደራሽነቱንም የሚያረጋግጥ መሆኑን አንስተዋል።

የዓለም የወተት ቀን የወተት ምርት ለሥነ-ምግብ እንዲሁም ለኢኮኖሚ ያለው ፋይዳ የሚታሰብበት ሲሆን፣ ዕለቱ በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የምግብ እና የግብርና ድርጅት (FAO) አማካኝነት እ.ኤ.አ በ2001 የተቋቋመ ዓለም አቀፍ ሁነት መሆኑ ይታወቃል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም