በሲዳማ ክልል የተገልጋይ እርካታን ለማሳደግ ለሪፎርም ሥራዎች ትኩረት ተሰጥቷል - ኢዜአ አማርኛ
በሲዳማ ክልል የተገልጋይ እርካታን ለማሳደግ ለሪፎርም ሥራዎች ትኩረት ተሰጥቷል
ሀዋሳ፣ ግንቦት 28/2018 (ኢዜአ)፡-የመንግስት አገልግሎት አሰጣጥን በማዘመን የተገልጋይ እርካታን ለማሳደግ ለሪፎርም ሥራዎች ትኩረት መስጠቱን የሲዳማ ክልል ገንዘብ ቢሮ አስታወቀ።
ቢሮው በመንግስት አገልግሎትና አስተዳደር ሪፎርም ዓላማ ላይ ለባለድርሻ አካላት ያዘጋጀው የግንዛቤ ማስጨበጫ መድረክ በሃዋሳ ከተማ ተካሂዷል።
የቢሮው ሀላፊ አቶ ሀይሌ ሀርሲሳ ለኢዜአ እንደገለጹት በቢሮው የመንግስት አገልግሎትን ቀልጣፋ፣ ተደራሽና ፍትሀዊ ለማድረግ የአስተዳደር ሪፎርም ተግባራዊ ማድረግ አስፈላጊ ነው።
የሪፎርም ሥራው የበጀት ሥራዎችን በቴክኖሎጂ ተደግፎ ለማከናወን ጠቀሜታው የጎላ መሆኑንም አንስተዋል።
ቢሮው የክፍያ ስርዓቱ በኤሌክትሮኒክስ የሚከናወንበትን አሰራር በመዘርጋት አገልግሎቱን ከጥሬ ገንዝብ ንክኪ ነጻ በማድረግ ግልጸኝነትና ተጠያቂነት የማስፈን ሥራ መጀመሩንም ተናግረዋል።
በሲዳማ ክልል ገንዘብ ቢሮ የሪፎርም ቴክኒክ ቡድን አስተባባሪ አቶ ጌቱ በቀለ በበኩላቸው እንዳሉት በቢሮው ቀደም ሲል ይሰጡ የነበሩ አገልግሎቶች በሪፎርሙ ደረጃ ወጥቶላቸው እየተከናወኑ ይገኛሉ።
ሪፎርሙ የተቋሙን አሰራር እና የሠራተኛውን የመፈጸም አቅም በማሳደግ የህዝብ ተቀባይነትና አመኔታን ለመፍጠር የሚያስችል ነው ያሉት ደግሞ በገንዘብ ሚኒስቴር የሪፎርም ድጋፍ ቡድን ሀላፊ አቶ ይገዙ ዳባ ናቸው።
ተግባራዊ የሚደረገው የመንግስት አገልግሎትና አስተዳደር ሪፎርም ለዜጎች ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት ያስችላል ብለዋል።