ስምምነቱ የአርብቶ አደሮችን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጥና የአደጋ ተጋላጭነትን መቀነስ የሚያስችል ነው - ኢዜአ አማርኛ
ስምምነቱ የአርብቶ አደሮችን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጥና የአደጋ ተጋላጭነትን መቀነስ የሚያስችል ነው
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 27/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያና በአፍሪካ ልማት ባንክ መካከል የተፈረመው ስምምነት የአርብቶ አደሮችን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጥና የአደጋ ተጋላጭነትን መቀነስ የሚያስችል መሆኑን በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግስት ዋና ተጠሪ ሚኒስትር ተስፋዬ በልጅጌ (ዶ/ር) ገለጹ።
የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ 6ኛው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በ5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን በ23ኛ መደበኛ ስብሰባው የተለያዩ አዋጆችን መርምሮ አጽድቋል።
በምክር ቤቱ የመንግስት ዋና ተጠሪ ሚኒስትር ተስፋዬ በልጅጌ (ዶ/ር) በኢትዮጵያና በአፍሪካ ልማት ባንክ መካከል የተፈረመው የአርብቶ አደሮች የኑሮ ዘይቤ ማሻሻያ ፕሮጀክት ማስፈጸሚያ የሚውል የብድር ስምምነት እና በኢትዮጵያና በዓለም አቀፍ የልማት ማህበር 6ኛው ምዕራፍ የልማታዊ ሴፍትኔት ማስፈጸሚያ ፕሮጀክት የተደረገ የብድር ስምምነት ረቂቅ አዋጆችን አስፈላጊነት በተመለከተ ለምክር ቤቱ ማብራሪያ አቅርበዋል።
የአርብቶ አደሮች የምግብና የኑሮ ዘይቤ ማሻሻያ ፕሮጀክት ማስፈጸሚያ የሚውለው የብድር ስምምነት ከኢትዮጵያ የብድር ስትራቴጂ ጋር የሚጣጣም ነው ብለዋል።
ስምምነቱ የአርብቶ አደሮችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጥ፣ ለግብርና፣ ለመስኖ ልማት፣ የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋምና የአደጋ ተጋላጭነትን መቀነስ የሚያስችል መሆኑን ገልጸዋል።
ለውሃ መሰረተ ልማት፣ ለእንስሳት ጤና አገልግሎት፣ ለዘላቂ የመሬት አያያዝ፣ ለአየር ትንበያ ጣቢያዎችና ለሌሎች መሰረተ ልማቶች ማስፋፊያ እንደሚውልም ጠቅሰዋል።
ምክር ቤቱ በረቂቅ አዋጁ ላይ በጥልቀት ከተወያየ በኋላ ረቂቅ አዋጁን በሙሉ ድምጽ አጽድቋል።
በሌላ በኩል በኢትዮጵያና በዓለምአቀፍ የልማት ማህበር 6ኛው ምዕራፍ የልማታዊ ሴፍትኔት ማስፈጸሚያ ፕሮጀክት የተደረገው የብድር ስምምነት ሴቶችና ወጣቶችን ተጠቃሚ የሚያደርግ መሆኑን ተናግረዋል።
በተለይም በኑሮ ማሻሻል፣ በምግብ ዋስትና እና በማህበራዊ ጥበቃ ሰርዓት እየተከናወኑ ካሉ ብሔራዊ የልማት ፕሮጀክቶች ጋር የተናበበ በመሆኑ ሚናው የጎላ ነው ብለዋል።
የምክር ቤቱ አባላት የብድር ስምምነቶቹ በግብርና፣ በመስኖ ልማት፣ በአየር ንብረት ለውጥ መቋቋምና የአደጋ ተጋላጭነትን በመቀነስ የዜጎችን ኑሮ ለማሻሻል የተጀመሩ ሥራዎችን እንደሚያጠናክሩ ጠቁመዋል።
ስምምነቶቹ በአግባቡ እንዲተገበሩና የታለመውን ግብ እንዲያሳኩ ድጋፍና ክትትል ማድረግ እንደሚገባም ተናግረዋል።
ምክር ቤቱ የስምምነት ረቂቅ አዋጆች ላይ በዝርዝር በመወያየት በአብላጫ ድምጽ አጽድቋቸዋል።
በሌላ በኩል የፌዴራል ታክስ አስተዳደር ማሻሻያ ረቂቅ አዋጅን፣ የግብርና ቢዝነስ ኩባንያ ረቂቅ አዋጅን፣ የምግብ ስርዓትና ስርዓተ ምግብ ረቂቅ አዋጅን፣ የኢትዮጵያ የካርበን ገበያ ረቂቅ አዋጅን እና የኢትዮጵያ ስታትስቲክስ ረቂቅ አዋጆች ቀርበው ውይይት ከተደረገባቸው በኋላ ለሚመለከታቸው ቋሚ ኮሚቴዎች ተመርተዋል።