ተቋማት የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂን ሙሉ በሙሉ ተግባራዊ እንዲያደርጉ የሚያስችል ድጋፍ እየተደረገ ነው - ኢዜአ አማርኛ
ተቋማት የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂን ሙሉ በሙሉ ተግባራዊ እንዲያደርጉ የሚያስችል ድጋፍ እየተደረገ ነው
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 26/2018(ኢዜአ)፦ የመንግሥት ተቋማት የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂን ሙሉ በሙሉ ተግባራዊ እንዲያደርጉ የሚያስችል ድጋፍ አጠናክሮ መቀጠሉን የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ገለጸ።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በታህሳስ ወር 2018 ዓ.ም ይፋ ያደረጉት “የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ” ሀገሪቱ በቴክኖሎጂ የታገዘ ሁለንተናዊ ብልጽግናን ለማረጋገጥ የያዘችውን ራዕይ የሚያሳይ ብሔራዊ ፍኖተ-ካርታ ነው።
ስትራቴጂው በቀጣዮቹ አምስት ዓመታት የ5ጂ ኔትወርክን ሙሉ በሙሉ ተደራሽ ለማድረግ፣ የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያን ለማስፋፋት እንዲሁም ዜጎችን በዲጂታል ክህሎት ለማብቃት ያተኮረ ነው።
በተጨማሪም ሀገሪቱን ከቴክኖሎጂ ተጠቃሚነት ወደ ቴክኖሎጂ ፈጣሪነት በማሸጋገርና ሰፊ የዲጂታል የሥራ ዕድሎችን በመፍጠር በኩል ፋይዳው የጎላ ነው።
በኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር የዲጂታል ኢኮኖሚ ዘርፍ መሪ ሥራ አስፈፃሚ ስዩም መንገሻ ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ቀደም ሲል በዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ የተመዘገቡ አበይት ስኬቶችንና የተገኙ ልምዶችን መሰረት በማድረግ አዳዲስ የዲጂታል እድገቶችንና ስኬቶችን እያስመዘገበ ይገኛል።
በዲጂታል 2025 ስትራቴጂ በሀገሪቱ ትልልቅና ስር ነቀል ለውጦች መምጣታቸውን አስታውሰው፤ ለዚህም ለአብነት ያህል በርካታ የወረቀት ስራ የሚጠይቁና የተንዛዙ የመንግስት አገልግሎቶች ወደ ዲጂታል አገልግሎት እንዲገቡ መደረጉን ጠቅሰዋል።
ይህ የተጀመረው ሀገራዊ የሪፎርም ጉዞ ይበልጥ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ትልቅ ሚና እየተጫወተ መሆኑን አብራርተዋል።
በአሁኑ ወቅት የተለያዩ ተቋማትና ሴክተሮች ቴክኖሎጂን ማዕከል አድርገው ያቀዷቸውን ስልታዊ ዕቅዶች ወደ ተጨባጭ ተግባር እየለወጡና በዚህም ዘርፈ-ብዙ ለውጦች እየታዩ መሆኑን ገልጸዋል።
በዚህም ተቋማቱ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂን ሙሉ በሙሉ ተግባራዊ እንዲያደርጉ የሚደረገውን ድጋፍ አጠናክሮ መቀጠሉን አስታውቀዋል።
የአምስት ሚሊየን ኢትዮ-ኮደርስ መርሐ-ግብር የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂን ስኬት ወደ መሬት የሚያወርድና ብሔራዊ ራዕዩን በተግባር የሚሸከም ግንባር ቀደም አስቻይ ሞተር ነው፡፡
ኢዜአ ያነጋገራቸው የአምስት ሚሊዮን ኢትዮ ኮደርስ ሥልጠና የወሰዱ ዜጎች ስልጠናው ከዘመኑ ጋር አብረን መራመድ የሚያስችለንን የዲጂታል ክህሎት እንድናጎለብት ምቹ ሁኔታ ፈጥሮልናል ብለዋል፡፡
የኮደርስ ስልጠናው ተጠቃሚ ቀለሙ ዘለቀ ኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ብዙ ተጨማሪ እውቀቶችን እንዲያገኝ እድል እንደፈጠረለት ገልጾ፤ ሁሉንም አይነት ኮርሶች በመውሰድ የምስክር ወረቀት እንዳገኘና በዲጂታል ቴክኖሎጂ በመታገዝ ስራዎቹን እያከናወነ መሆኑን ተናግሯል።
ሌላኛዋ የስልጠናው ተጠቃሚ ሶስና አወል በበኩሏ የአምስት ሚሊየን የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና መውሰዷንና ከስራዋ ጋር በቀጥታ ግንኙነት ያላቸው በመሆናቸው ለስራዋ እጅግ እያገዛት መሆኑን ገልጻለች።
በአምስት ሚሊየን ኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ተጨማሪ የሆነ እውቀት በማግኘት የዲጂታል ክህሎቱን ማሳደግ መቻሉንና የምስክር ወረቀት ማግኘቱን የተናገረው ደግሞ የስልጠናው ተጠቃሚ መሀመድ ጀማል ነው።