ቀጥታ፡

በኢትዮጵያ በሁሉም መስክ የዜጎችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚነት የሚያረጋግጥ ስኬታማ አቅም እየተገነባ ነው

አዲስ አበባ፤ግንቦት 25/2018 (ኢዜአ)፦በኢትዮጵያ በሁሉም መስክ የዜጎችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚነት የሚያረጋግጥ ስኬታማ አቅም እየተገነባ መሆኑን የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪያት ካሚል ገለጹ።  

የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር እና የኢትዮጵያ ልማት ባንክ በፋይናንስ አቅርቦት የዜጎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ማጠናከር የሚያስችል የመግባቢያ ስምምነት ተፈራርመዋል።

በሥራ ዕድል ፈጠራና ክህሎት ልማት ማበረታቻ የፋይናንስ አቅርቦት የትብብር ስምምነቱን የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪያት ካሚል እና የኢትዮጵያ ልማት ባንክ ፕሬዝዳንት ኢሳያስ ካሳ (ዶ/ር) ፈርመውታል።


 

የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪያት ካሚል በዚሁ ወቅት፤ ኢትዮጵያ የዜጎቿን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት በሚያረጋግጥ የተቃና ጉዞ ላይ ናት ብለዋል።

የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ ብልፅግና ለማረጋገጥም የወጣቱን ዕምቅ የፈጠራ ሃሳብና አቅም ወደ ተግባር የሚለውጥ ውጤታማ ሥራ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል።

የተቋማት ትብብርም ሁለንተናዊ ሉዓላዊነትን ያረጋገጠች ጠንካራ ኢትዮጵያን ለመገንባት ጉልህ ሚና እንደሚጫወት አንስተዋል።

የተቋማቱ የትብብር ስምምነትም የሥራ ፈጣሪ ወጣቶችን የፈጠራ ክህሎት የሚያዳብር የፋይናንስ አቅርቦት በማመቻቸት የነገ ተስፋቸውን ምቹ ምኅዳር የሚፈጥር መሆኑን ተናግረዋል።


 

ለአብነትም ኢትዮጵያ በሁሉም መስክ የዜጎችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚነት በማረጋገጥ የአምራችነት ባህልን የሚገነባ አስቻይ ሁኔታ እየፈጠረች መሆኗን እንደሚያሳይ ጠቅሰዋል።

የኢትዮጵያ ልማት ባንክ ፕሬዚዳንት ኢሳያስ ካሳ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ስምምነቱ በተለያዩ ክልሎች በግብርና ዘርፍ ላይ የተሰማሩ ወጣቶችን የፋይናንስና የግብዓት አቅርቦት የሚያሳድግ ነው ብለዋል።

የተቋማቱ ትብብር ስምምነትም የሴቶችና ወጣቶችን የፋይናንስና የግብዓት አቅርቦት አቅም በማሳደግ ከፍተኛ የወለድ መጠን ቅናሽ የተደረገበት መሆኑን ገልጸዋል።


 

በሥራና ክህሎት ሚኒስቴር የግብርና ኢንተርፕራይዞች ልማት ለሥራ ዕድል ፈጠራ ፕሮጀክት አስተባባሪ አሽቅ በድሩ፤ ፕሮጀክቱ በሀገር አቀፍ ደረጃ የሚተገበርና የዜጎችን የግብርና ምርታማነት የሚያሻሽል የፋይናንስና የግብዓት አቅርቦት የሚያስገኝ ነው ብለዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም