የመስኖ ግድቦች ከተረጂነት ወደ ምርታማነት ለመሸጋገር የሚደረገውን ጉዞ እያፋጠኑ ነው - ኢዜአ አማርኛ
የመስኖ ግድቦች ከተረጂነት ወደ ምርታማነት ለመሸጋገር የሚደረገውን ጉዞ እያፋጠኑ ነው
ነገሌ ቦረና፣ግንቦት 20/2018 (ኢዜአ)፦በምሥራቅ ቦረና ዞን አነስተኛና መካከለኛ የመስኖ ግድቦች ከተረጂነት ወደ ምርታማነት ለመሸጋገር የሚደረገውን ጉዞ እያፋጠኑ መሆኑን የዞኑ መስኖና አርብቶ አደር ጽሕፈት ቤት ገለጸ።
የምሥራቅ ቦረና ዞን አብዛኛው ነዋሪ ሕይወትና መተዳደሪያው አርብቶ አደርነትና ከአነስተኛ የእርሻ ሥራ ጋር የተያያዘ ነው።
አካባቢው በተደጋጋሚ ጊዜ በሚከሰት ድርቅና በተለዋዋጭ የአየር ንብረት መዛባት ምክንያት ከፍተኛ የሆነ የውኃ እጥረት ሲያጋጥመው ቆይቷል።
ይህንን ለመፍታት ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ትኩረት የተሰጠው አነስተኛና መካከለኛ የመስኖ መሠረተ ልማቶችን ማስፋፋት ላይ ነው።
የመስኖ ግድቦቹ መገንባት ማኅበረሰቡ መደበኛውን የዝናብ ወቅትን ብቻ ከመጠበቅ ወጥቶ፣ ያለውን የከርሰ ምድርና የገፀ ምድር ውኃ በአግባቡ በመጠቀም በዓመት ሁለትና ሦስት ጊዜ እንዲያመርት ዕድል ፈጥሯል።
የዞኑ መስኖና አርብቶ አደር ጽሕፈት ቤት እንዳስታወቀው፤በዞኑ ቆላማ ወረዳዎች የተገነቡ ሁለት የመስኖ መሠረተ ልማቶች እየሰጡ ባለው አገልግሎት ዘርፈ ብዙ ጥቅም እያስገኙ ነው።
በጽሕፈት ቤቱ የዲዛይንና ቁጥጥር ቡድን መሪ ኢንጂነር ተስፋሁነኝ ዳንኤል እንደገለጹት፤ ፕሮጀክቶቹ በተለይም ከተረጂነት ወደ ምርታማነት በሚደረገው ሽግግር ውስጥ ትልቅ እገዛ እያደረጉ ነው።
በተለይም በዞኑ በሊበንና በጎሮዶላ ወረዳዎች የተገነቡት ግድቦቹ ነዋሪውን ወደ መስኖ ልማት ማስገባት ያስቻሉ ሲሆን ለምርታማነት ዕድገትም አስተዋጽኦ እያበረከቱ ነው ብለዋል።
እነዚህ የመስኖ ፕሮጀክቶች ከ8 ነጥብ 3 ሚሊዮን ሜትር ኪዩብ በላይ የዝናብ ውኃ የማጠራቀም አቅም እንዳላቸውም ገልጸዋል።
የመስኖ ፕሮጀክቶቹ ከ465 ሄክታር በላይ መሬትን በዘመናዊ መስኖ ከማልማት ጎን ለጎን፣ የአካባቢውን የመኖና የውኃ ችግር የሚያቃልሉ መሆናቸውንም አስረድተዋል።
በተጨማሪም ግድቦቹ ለአሳ ሀብት ልማትና ለቱሪዝም መዳረሻነት አገልግሎት እንዲሰጡ ተደርገው የተገነቡ መሆናቸውን ጠቁመው፤ ለአብነትም በዞኑ ድቤ አዳማ መስኖ ፕሮጀክት ግድብ ውስጥ እስካሁን ከ10 ሺህ በላይ የአሳ ጫጩቶች መለቀቃቸውን ገልጸዋል።
ኢዜአ ያነጋገራቸው የዞኑ ነዋሪዎች እንዳሉት፥የመስኖ ፕሮጀክቶቹ በዘመናዊ መስኖ ልማት የምግብ ዋስትናቸውን ለማረጋገጥ ያግዛቸዋል።
በዞኑ ሊበን ወረዳ የሲሚንቆ ቀበሌ ነዋሪ አቶ ቃሲም ገመዳ እንደገለጹት፤ አካባቢው በድርቅና በዝናብ እጥረት ሳቢያ በተደጋጋሚ የመኖና የውኃ ችግር ያጋጥመው ነበር።
ቀደም ሲል መኖና ውኃ ፍለጋ ከአንድ ቦታ ወደ ሌላ ቦታ በሚያደርጉት እንቅስቃሴ ለከፍተኛ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮች ሲጋለጡ መቆየታቸውንም ያስታውሳሉ።
በአካባቢያቸው በተገነባው የመስኖ ፕሮጀክት የበጋ ስንዴን በዘመናዊ መስኖ በማልማት የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እንዲሁም የእንስሳት መኖና የውኃ ችግርን ለማቃለል እንደሚያግዝ ጠቁመው፥የበጋ ስንዴ፣ ቲማቲም፣ድንችና ሽንኩርት በመስኖ ለማልማት ተዘጋጅተዋል።
ሌላው ነዋሪ አቶ ጉዮ ጃተኒ በበኩላቸው፤ ቀደም ሲል መደበኛ ሥራቸውን ትተው የእንስሳት መኖና የመጠጥ ውኃ ፍለጋ ሩቅ መንገድ ይጓዙ እንደነበር ያስታውሳሉ።
በአካባቢያቸው የተገነቡት የመስኖ ፕሮጀክቶች ከአካባቢያቸው ሳይርቁ የበጋ ስንዴ በማምረት ችግሩን በዘላቂነት ለመቋቋም እንዳስቻላቸው ገልጸዋል።