የቴፒ ግብርና ምርምር ማዕከል በምርምር ያወጣቸውን ችግኞች ለአርሶ አደሩ እያሰራጨ ነው - ኢዜአ አማርኛ
የቴፒ ግብርና ምርምር ማዕከል በምርምር ያወጣቸውን ችግኞች ለአርሶ አደሩ እያሰራጨ ነው
ሚዛን አማን፤ ግንቦት 20/2018(ኢዜአ)፦ የቴፒ ግብርና ምርምር ማዕከል በምርምር ያወጣቸውን የቡና፣ የቅመማቅመም እና የፍራፍሬ ችግኞች ለአርሶ አደሮች እያሰራጨ መሆኑን ገለጸ።
ማዕከሉ በገበያ ተፈላጊ የሆኑ የካካዎ፣ የቫኔላና ሌሎች የቅመማቅመም ችግኞችን ለመጪው ክረምት ተከላ ለአርሶ አደሮች እያሰራጨ መሆኑን አስታውቋል።
የቴፒ ግብርና ምርምር ማዕከል ዳይሬክተር ደረጀ ቱሉ (ደ/ር) እንዳሉት፣ ማዕከሉ የአርሶ አደሩን ምርታማነት የሚያሻሽሉና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን የሚያሳድጉ ከ70ዐ ሺህ በላይ የቅመማቅመም ችግኞችን እያዘጋጀ ይገኛል።
ችግኞቹ በመጪው ክረምት የሚተከሉ ሲሆን ለአካባቢ ሥነ ምህዳር ተስማሚና ምርታማነታቸው በምርምር የተረጋገጡ መሆናቸውን ገልጸዋል።
በክረምቱ የሚተከሉ ችግኞች ምርታማነታቸው ከፍ ያለ ከመሆኑ በላይ የአካባቢው ሥነ ምህዳር ለመጠበቅ ተደማሪ አቅም እንደሚሆኑም አስረድተዋል።
የሸካ ዞን ግብርና፣ ደን፣ አካባቢ ጥበቃና ኅብረት ሥራ መምሪያ ምክትል ኃላፊ አለምሰገድ ኃይለኢየሱስ በበኩላቸው ማዕከሉ ምርታማነታቸው በምርምር የተረጋገጡ የቅመማቅመምና ሌሎች ችግኞችን ለአርሶ አደሩ ማቅረቡን ተናግረዋል።
በዚህም የአርሶ አደሩን ምርታማነት በማሳደግ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነቱን ለማሳደግ እንደቻለ አክለዋል።
ተግባሩን በማስቀጠልም ማዕከሉ በበጋ ወራት ያፈላቸውን ችግኞች ለክረምቱ ወቅት ተከላ ለአርሶ አደሮች እያሰራጨ መሆኑንም ገልጸዋል።
በዞኑ የየኪ ወረዳ አርሶ አደር መሐመድ ታዬ እና አርሶ አደር አየለች አናሞ በበኩላቸው ከምርምር ማዕከሉ የሚቀርቡ ዝርያዎች በአጭር ጊዜ ውስጥ ምርት የሚሰጡና ምርታማነታቸው ያደገ መሆኑን በተግባር ማረጋገጣቸውን ተናግረዋል።
ዘንድሮ በራሳቸው ያዘጋጁትንና በማዕከሉ የተዘጋጁ ችግኞችን በመትከል ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ ወደ ሥራ መግባታችውን አመልክተዋል።