ከተማ አስተዳደሩ የቤተሰብ ብልጽግናን ለማረጋገጥ የሚያስችሉ የልማት ፕሮጀክቶችን በልዩ ትኩረት እያከናወነ ነው - ኢዜአ አማርኛ
ከተማ አስተዳደሩ የቤተሰብ ብልጽግናን ለማረጋገጥ የሚያስችሉ የልማት ፕሮጀክቶችን በልዩ ትኩረት እያከናወነ ነው
አዳማ፤ ግንቦት 18/2018 (ኢዜአ)፡- የአዳማ ከተማ አስተዳደር የቤተሰብ ብልጽግናን ለማረጋገጥ የሚያስችሉ የልማት ፕሮጀክቶችን በልዩ ትኩረት እያከናወነ መሆኑን የከተማው ከንቲባ አቶ ኃይሉ ጀልዴ ገለጹ።
በአዳማ ከተማ በ17 ነጥብ 3 ቢሊዮን ብር ወጪ የተገነቡ የልማት ፕሮጀክቶች ተመረቁ።
የልማት ፕሮጀክቶቹን በዛሬው ዕለት በይፋ የመረቁት የአዳማ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ኃይሉ ጀልዴ እና የኦሮሚያ ክልል ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ ሮዛ አባቢያ ናቸው።
በምረቃ መርሃ ግብሩ ላይ አቶ ኃይሉ ጀልዴ እንደገለጹት፤ በበጀት ዓመቱ የቤተሰብ ብልጽግናን፣ የሥራ ዕድል ፈጠራን፣ የገበያ ማረጋጋትንና ማኅበራዊ አገልግሎትን ማዕከል ያደረጉ በርካታ የልማት ሥራዎች ሲከናወኑ ቆይተዋል።
በመጀመሪያው የምረቃ ምዕራፍ ዛሬ ከተመረቁት መካከል የመንግስትንና የሕዝብን አቅም በማቀናጀት በ5 ነጥብ 9 ቢሊዮን ብር በጀት የተገነቡ 14 የልማት ፕሮጀክቶች ይገኙበታል ብለዋል።
እነዚህ ፕሮጀክቶች በትምህርት፣ በጤና፣ በመንገድ መሠረተ ልማት እና በሕዝብ መድኃኒት ቤቶች ላይ ያተኮሩ መሆናቸውን ጠቅሰዋል።
ከእነዚህም በተጨማሪ የቤተሰብ ብልጽግናን ለማረጋገጥ የሚያስችሉ 8 ሺህ ሼዶች በ11 ቢሊዮን ብር ተገንብተው በማኅበር ለተደራጁ ቤተሰቦችና ወጣቶች እየተላለፉ መሆኑን አመልክተዋል።
በከተማዋ ኢንዱስትሪ መንደር የተገነቡት እነዚህ ሼዶች ለእንስሳት ማድለብ፣ ለወተት ላም እርባታ፣ ለፍየል ማሞከት፣ ለአሳማና ዶሮ እርባታ እንዲሁም ለሌሎችም ልማቶች አመቺ መሆናቸውን ገልጸዋል።
በሼዶቹ አማካኝነት ከ80 ሺህ በላይ በኢንተርፕራይዝ የተደራጁ ወጣቶችና አንቀሳቃሾች ተጠቃሚ መሆናቸውን ከንቲባው አስታውቀዋል።
አስተዳደሩ ለሥራ ዕድል ፈጠራ የመሥሪያ ቦታ ከማመቻቸት ባለፈ፣ 3 ነጥብ 1 ቢሊዮን ብር የባንክ ብድር እንዲያገኙ በቅንጅት መሥራቱንም ገልጸዋል።
ለልማት ፕሮጀክቶቹ ስኬታማነት የከተማው ሕዝብ ላደረገው ከፍተኛ ተሳትፎ ምስጋና ያቀረቡት ከንቲባ ኃይሉ፤ የተጀመሩ የልማት ሥራዎች ተጠናክረው እንዲቀጥሉ ሕዝቡ በልማት ሥራዎች ላይ በንቃት እንዲሳተፍ ጥሪ አቅርበዋል።
በምረቃ መርሃ ግብሩ ላይ የተገኙት የኦሮሚያ ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ ሮዛ አባቢያ በበኩላቸው፤ በመንግስት በጀትና በሕዝብ ተሳትፎ የተገነቡና ሕዝብን ማዕከል ያደረጉ ፕሮጀክቶች፣ የለውጡ መንግስት ለሕዝብ የገባውን ቃል በተግባር የሚያሳይ መሆኑን ማረጋገጫ ናቸው ብለዋል።
በአዳማ የተመረቁት ፕሮጀክቶች ለከተማው ማኅበረሰብ ዘርፈ ብዙ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ የሚያጎናጽፉ ከመሆናቸውም በላይ፣ የአስተዳደሩን ፕሮጀክቶች ጀምሮ የማጠናቀቅ ግብ በተግባር የሚያሳዩ ሕያው ምስክሮች መሆናቸውን ገልጸዋል።
ቀደም ሲል የመሠረተ ድንጋይ የተቀመጠላቸው በርካታ ፕሮጀክቶች እውን ሳይሆኑ የሕዝብ የቅሬታ ምንጭ ሆነው መቆየታቸውን አስታውሰው፤ የለውጡ መንግስት በወሰደው ቁርጠኝነት በርካታ የተጓተቱና አዳዲስ ፕሮጀክቶች በክልሉ ተገንብተው ሕዝቡን ተጠቃሚ ማድረግ መቻላቸውን አብራርተዋል።
በዚህ በጀት ዓመትም ለሕዝቡ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ መረጋጋት ወሳኝ የሆኑ በርካታ ፕሮጀክቶች መገንባታቸውን የጠቀሱት ወይዘሮ ሮዛ፤ የተገነቡት ከ21 ሺህ በላይ ፕሮጀክቶች በየደረጃው የሚገኙ የነዋሪዎችን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ መሆናቸውን አውስተዋል።
በምረቃ መርሃ ግብሩ ላይ የክልሉና የከተማዋ አስተዳደር ከፍተኛ አመራሮች፣ ነዋሪዎችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።