ቀጥታ፡

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ለአፍሪካ ቀን የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላለፉ

አዲስ አበባ፤ ግንቦት 17/2018 (ኢዜአ)፦ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ለመላው አፍሪካውያን ወንድሞችና እህቶች ለአፍሪካ ቀን የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትሩ ባስተላለፉት መልዕክት፥ ከ63 ዓመታት በፊት የአፍሪካ አባቶች እዚሁ አዲስ አበባ ላይ በመሰብሰብ ነፃ እና የተባበረች አህጉርን የመገንባት ታላቅ ህልም ማለማቸውን አስታውሰዋል።

ይህ የአባቶች የአንድነት ህልም ዛሬም ድረስ ሳይደበዝዝ በደማቅ ሁኔታ መቀጠሉን ገልጸዋል።

ኢትዮጵያ የአፍሪካ ህብረት ታሪካዊ ማዕከል መሆኗን የጠቀሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ዛሬም በዚያው በታሪካዊው የአንድነት መንፈስ ከእያንዳንዱ የአፍሪካ አገር ጋር በጋራ ለመቆም ያላትን ቁርጠኝነት አረጋግጠዋል።

ይሁን እንጂ አህጉሪቱን ለማበልጸግ የሚከናወኑ ተግባራት ገና ብዙ መሆናቸውን ጠቁመው፤ አሁን ካሉበት ደረጃ ይበልጥ ለመሻገር ከቃላት ወደ ተግባር፣ከቃል ኪዳንም ወደ ተጨባጭ ዕድገት መሸጋገር እንደሚያስፈልግ አሳስበዋል።

የአፍሪካ ታላቁ እና ዋነኛው ሀብት ምንጊዜም ቢሆን ሕዝቦቿ መሆናቸውን የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ አህጉሪቱ ያላትን እምቅ አቅም በመጠቀም በአንድነት የላቀ ከፍታ ላይ እንደርሳለን ሲሉ ገልጸዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም