የኢትዮጵያ የባህር በር ጥያቄ ታሪካዊና ሕጋዊ መሰረት ያለው፤ ለቀጣናዊ ትስስር እና የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነት የላቀ ሚና አለው - ኢዜአ አማርኛ
የኢትዮጵያ የባህር በር ጥያቄ ታሪካዊና ሕጋዊ መሰረት ያለው፤ ለቀጣናዊ ትስስር እና የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነት የላቀ ሚና አለው
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 15/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የባህር በር ጥያቄ ታሪካዊና ሕጋዊ መሰረት ያለው፤ ለቀጣናዊ ትስስር እና የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነት የላቀ ሚና እንዳለው የዘርፉ ምሁራን አስገነዘቡ።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ቀደም ሲል፤ የቀይ ባህር ጉዳይ ለኢትዮጵያ ሕጋዊ፣ ታሪካዊ፣ መልክዓ ምድራዊ (ጂኦግራፊያዊ) እና ኢኮኖሚያዊ ጥያቄ መሆኑን መግለጻቸው ይታወሳል።
ኢትዮጵያ የባህር በር ያጣችበት መንገድ ሕጋዊና ተቋማዊ መሰረት እንደሌሎው የጠቆሙት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ኢትዮጵያና ቀይ ባህር ለዘለዓለም ተነጣጥለው ሊኖሩ እንደማይችሉና ጥያቄው በፍትሐዊ፣ በሰላማዊ፣ በሰጥቶ መቀበል መርህ ምላሽ እንዲያገኝ የሚደረገው ጥረት እንደሚቀጥል ማስታወቃቸው ይታወሳል።
የኢትዮጵያ ፐብሊክ ሰርቪስ ዩኒቨርሲቲ የአመራርና አስተዳደር ኮሌጅ ምክትል ዲን መሀመድ አሊ (ዶ/ር)፤ ኢትዮጵያ በአፍሪካ ቀንድና በቀጣናው ላይ ከፍተኛ የሰላም ማስከበር ሚና ስትጫወት የቆየችና አሁንም ይህንኑ እያደረገች ያለች ሀገር መሆኗን ገልጸዋል።
በተለይም በሰላም ማስከበር የሰለጠነ የሰው ኃይል በማሰማራት፣ መስዋዕትነት ጭምር እየከፈለች የአካባቢውን ሰላምና ጸጥታ በማስከበር በኩል ትልቅ አስተዋጽኦ እያበረከተች መሆኗን አብራርተዋል።
ይህ የሰላም ማስከበር ልምዷ በቀይ ባህር ቀጣና ላይ ካላት ስትራቴጂካዊ ጥቅም ጋር ቀጥተኛ ቁርኝት እንዳለውም ገልጸዋል፡፡
የኢትዮጵያ አጠቃላይ የወጪና ገቢ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ መሰረት ያደረገው ቀይ ባህርን መሆኑን አመልክተው፤ በዚሁ ቀጣና ሀገሪቱ የተለየ ፍላጎትና ጥቅም ሊኖራት እንደሚገባ አስረድተዋል።
የኢትዮጵያ ወደ ባህር በር መመለስ ለጎረቤት ሀገሮችም ጭምር የጋራ ጥቅም እንዳለው የቀጣናው ሕዝቦች እንዲገነዘቡ ማድረግ ያስፈልጋል ያሉት ምሁሩ፤ አካባቢው ላይ አስተማማኝ ሰላምና ጸጥታ እንዲሰፍን ኢትዮጵያ ትልቁን ሚና እንደምትጫወት ተናግረዋል።
ይህም ጠቃሚነቱ ለአንድ ሀገር ብቻ ሳይሆን ለሁሉም ጎረቤት ሀገሮች እንደሚሆን ማሰብ ይገባል ብለዋል።
በቀጣናው የሚኖረው ማህበረሰብ በቋንቋ፣ በእምነት፣ በባህልና በኢኮኖሚ በከፍተኛ ደረጃ የተሳሰረ መሆኑን ጠቁመው፤ ይህንን ቀጣናዊ ትስስር አጠናክሮ የመቀጠል ጥቅም አጠቃላይ የቀጣናው ሕዝብ እንዲገነዘበው የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነትን በማጠናከር በኩል በትኩረት መስራት እንደሚገባ አስገንዝበዋል።
በጋምቤላ ዩኒቨርሲቲ የዓለም አቀፍ ግንኙነት ረዳት ፕሮፌሰር ናርዶስ ሃዋዝ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የቀይ ባህር ጉዳይ ሁል ጊዜም ቢሆን የታሪካዊ ባለቤትነት ጥያቄን አብሮ የሚያስነሳ መሆኑን ጠቁመዋል።
የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነትን ለማረጋገጥ የምታደርገው ዲፕሎማሲያዊ ጥረት ትልቁ ሚናውና ማጠንጠኛው ከዚሁ ታሪካዊ እውነታ ጋር የተያያዘ መሆኑን ገልጸዋል።
በመንግሥታት ደረጃ የሚደረገው ዲፕሎማሲያዊ ንግግርና ውይይት እንደተጠበቀ ሆኖ ኢትዮጵያ በአፍሪካ ቀንድ ድንበር ተሻጋሪ የሆኑ የሕዝቦች የጋራ ማንነት၊ ባህልና ታሪክ መኖሩንና በእነዚህ ሕዝቦች መካከል ባለው ትስስር ላይ የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነትን በማጠናከር መቀራረብን ይበልጥ ማሳደግ እንደሚገባ ተናግረዋል።
ይህ የሕዝብ ለሕዝብ ትስስር ደግሞ ውሎ አድሮ ቀጣናውን በራሱ ጊዜ ወደ አንድ የተዋሃደ ማህበረሰብ ሊመራው እንደሚችልም አመልክተዋል።