የለውጡ መንግስት ባከናወነው የሪፎርም ስራ ለፈተናዎች የማይበገር ብቃቱ የተረጋገጠ የሀገር መከላከያ ሰራዊት ተገንብቷል - ኢዜአ አማርኛ
የለውጡ መንግስት ባከናወነው የሪፎርም ስራ ለፈተናዎች የማይበገር ብቃቱ የተረጋገጠ የሀገር መከላከያ ሰራዊት ተገንብቷል
ሃዋሳ፤ ግንቦት 15/2028 (ኢዜአ)፡- የለውጡ መንግስት ባከናወነው የሪፎርም ስራ ለፈተናዎች የማይበገር ብቃቱ የተረጋገጠ የሀገር መከላከያ ሰራዊት መገንባት መቻሉን የመከላከያ ሚኒስትር ኢንጂነር አይሻ መሃመድ ገለጹ፡፡
የመከላከያ ሰራዊት ፋውንዴሽን ለመከላከያ ሰራዊት አባላትና ለቋሚ ሲቪል ሰራተኞቹ በሃዋሳ ያስገነባቸውን 232 የጋራ መኖሪያ ቤቶች በእጣ የማስተላለፍ መርሃ ግብር አከናውኗል፡፡
በወቅቱም ሚኒስትሯ አይሻ መሃመድ (ኢ/ር) እንደገለጹት፤ የለውጡ መንግስት ባከናወነው የሪፎርም ስራ በፈተናዎች የማይበገር ብቃቱ የተረጋገጠ የሀገር መከላከያ ሰራዊት መገንባት ተችሏል።
የለውጡ መንግስት እውን ባደረገው የሪፎርም ስራ መሰረት በወጣው የመከላከያ ሰራዊት አዋጅ የሰራዊቱን ክብር የሚመጥኑ ጥቅማ ጥቅሞች በሚገባ እንዲከበሩ ተደርጓል ብለዋል።
በዚህም ለሀገር ሉዓላዊነትና ለህዝብ ሰላም የህይወት መስዋዕትነት ለሚከፍል የመከላከያ ሰራዊት ጥቅም መከበር የሚደረግ ድጋፍ ውለታ ሳይሆን የክብር ግዴታ መሆኑን አንስተዋል፡፡
በመከላከያ ሰራዊት ፋውንዴሽን የተገነቡ የጋራ መኖሪያ ቤቶች መንግስትና ህዝብ ለሰራዊቱ ያላቸውን ምስጋናና ፍቅር በተግባር ያሳዩበትና ሀገራዊ ህሊና የወለዳቸው የእውቅና ውጤቶች ናቸው ሲሉ ገልጸዋል፡፡
ፕሮጀክቱ በአጭር ጊዜ እንዲጠናቀቅ የተደረገው የጋራ ርብርብ የኢትዮጵያውያንን የመደጋገፍና የአብሮነት ጥበብ ያሳየ መሆኑን የጠቀሱት ሚኒስትሯ የመኖሪያ ቤቶቹ ፋውንዴሽኑ በራሱ ባለሙያዎች የገነባው መሆኑንም አመልክተዋል፡፡
የጋራ መኖሪያ ቤቶቹ ግንባታ ሰራዊቱ ራሱንና ቤተሰቡን በተረጋጋ መንገድ በማኖር ሀገራዊ ግዳጁን በተገቢው እንዲወጣ የሚያደርግና ለሃዋሳ ከተማ ተጨማሪ ውበትና የልማት ውጤት መሆኑን ተናግረዋል፡፡
የሲዳማ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የትምህርት ቢሮ ሃላፊ አቶ በየነ በራሳ በበኩላቸው የመከላከያ ሰራዊት ለሀገር ሉአላዊነት፣ ክብርና ለህዝብ ሰላም በታማኝነት የሚያገለግልና የህይወት መስዋዕትነት የሚከፍል ነው ብለዋል፡፡
በዛሬው እለት የተመረቁ የጋራ መኖሪያ ቤቶች ከ820 ነጥብ 9 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ የተደረገባቸው መሆናቸውን የተናገሩት ደግሞ የመከላከያ ሚኒስቴር ፋውንዴሽን ዋና ስራ አስፈጻሚ ሜጀር ጄኔራል ደረጀ መገርሳ ናቸው፡፡
የጋራ መኖሪያ ቤቶቹ በአነስተኛ ወጪ በራስ አቅም የተገነቡ መሆናቸውን ጠቅሰው ሰራዊቱ ለሀገርና ለህዝብ ለሚከፍለው መስዋእትነት እውቅና የሚሰጡ በመሆናቸው ተግባሩ ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል፡፡
ከመኖሪያ ቤት ባለእድለኞች መካከል ሌተናል ኮሎኔል ታመነች ተሰማ እና ሌተናል ኮሎኔል አክሊሉ አሻንጎ የቤት ባለቤት በመሆናቸው ደስተኛ መሆናቸውን ገልጸው፤ መንግስት ሰራዊቱን የቤት ባለቤት ለማድረግ የጀመረው ስራ የሚደነቅ ነው ብለዋል፡፡
ይህም ሰራዊቱ ራሱንና ቤተሰቡን በተረጋጋ ሁኔታ እንዲመራና ግዳጁን በተገቢው እንዲወጣ የሚያስችልና ተስፋን የሚሰጥ መሆኑንም ተናግረዋል፡፡
በመርሃ ግብሩ ላይ የመከላከያ ሚኒስቴር ከፍተኛ አመራሮች፣ የተለያየ ማዕረግ ያላቸው የሰራዊት አባላትና ሌሎች እንግዶች ተገኝተዋል።