ቀጥታ፡

የአካባቢ ጸጋዎችን መሰረት ያደረጉ የሥራ ዕድል ፈጠራ ስራዎች ተጨባጭ ውጤት እያስመዘገቡ ነው

አዲስ አበባ፤ ግንቦት 15/2018(ኢዜአ)፦ በየአካባቢው የሚገኙ የፈጠራና የተፈጥሮ ጸጋዎችን በመለየትና የሥራ ዕድሎችን በማስፋፋት ተጨባጭ ውጤቶች እየተገኙ መሆኑን የተለያዩ ክልሎች የሥራና ክህሎት ቢሮ የሥራ ኃላፊዎች ገለጹ።

በኢትዮጵያ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ የሥራ ዕድል ፈጠራን ለማሳደግ፣ የግል ዘርፉን ለማበረታታትና የሥራ አጥነት ቁጥርን ለመቀነስ በርካታ መዋቅራዊና ሕጋዊ ሪፎርሞች ተከናውነዋል።

ለአብነትም የአምራች ኢንዱስትሪዎችን ማስፋፋት፣ ለሥራ ዕድል ቅድሚያ የሚሰጥ ስትራቴጂ ትግበራ፣ ተቋማዊ ሪፎርም እንዲሁም የውጭ ሀገር የሥራ ስምሪትን ማመቻቸት በዋናነት የሚጠቀሱ ተግባራት ናቸው።


 

የተለያዩ ክልሎች የሥራና ክህሎት ቢሮ ኃላፊዎች ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የአካባቢ ጸጋዎችን በጥናት በመለየት የሥራ ዕድልን ለማስፋፋት የተከናወኑ ተግባራት አበረታች ውጤቶችን አስገኝተዋል።

የአካባቢውን ጸጋ ተጠቅመው ዜጎች በማኅበረሰብና በቤተሰብ የንግድ ሥራዎች ላይ እንዲሰማሩ ምቹ ሁኔታዎች መፈጠራቸውን አመልክተው፤ የሥልጠና፣ የብድር እና የሌሎች ተያያዥ ድጋፎችን በማድረግ የዜጎች ውጤታማነት ይበልጥ እየጎለበተ መምጣቱን ተናግረዋል።

በኢትዮጵያ የሥራ ገበያ መረጃ ሥርዓት አማካኝነት የሥራ ፈላጊዎች ምዝገባና የሥራ ዕድል ፈጠራ መረጃዎችን በዘመናዊ መልኩ በማደራጀት፣ ቀልጣፋ፣ ግልጽና ተደራሽ አገልግሎት እየተሰጠ መሆኑን ኃላፊዎቹ ጠቁመዋል።


 

የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የሥራ ዕድል ፈጠራና ኢንተርፕራይዝ ልማት ቢሮ ምክትል ቢሮ ኃላፊ ተመስገን ኃይሌ፤ በክልሉ የሀገር ውስጥ የሥራ ዕድሎችን ለማሳደግ የአካባቢ ጸጋዎችን በመለየት ዜጎች ተጠቃሚ እንዲሆኑ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል።

በተያዘው በጀት ዓመትም ለዜጎች የክህሎት፣ የአቅም ግንባታና ሌሎች ድጋፎችን በማመቻቸት እና የሥራ ዕድል ፈጠራው ክህሎት መር በማድረግ እስካሁን ለ280 ሺህ ለሚሆኑ ዜጎች ቋሚ የሥራ ዕድል መፈጠሩን ጠቁመዋል፡፡


 

በሲዳማ ክልል ሥራና ክህሎት ቢሮ ምክትል ኃላፊ ከፍያለው ከበደ በበኩላቸው፤ በክልሉ በስፋት የሚገኙ ምርቶችን በመለየት የማኅበረሰብና የቤተሰብ የንግድ ሥራዎችን ከሌማት ትሩፋት መርሃ-ግብር ጋር በማስተሳሰር ውጤታማ ሥራዎች እየተከናወኑ እንደሚገኝ ገልጸዋል።


 

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ሥራና ክህሎት ቢሮ የሥራ ስምሪትና ገበያ ልማት ዘርፍ ኃላፊ ዘውዱ ሳሙኤል፤ በክልሉ የሥራ ዕድል ፈጠራ ትኩረት ያደረገው በአካባቢ ጸጋዎችና አቅሞች ላይ መሆኑን ተናግረዋል።

በዚህም ዜጎች ተደራጅተው በአካባቢው በሚገኙ ጸጋዎች ላይ እሴት በመጨመር በስፋት እንዲያመርቱና ወደ ገበያ እንዲያስገቡ በማድረግ በኩል ስኬታማ ሥራዎች መከናወናቸውን አስገንዝበዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም