ቀጥታ፡

የነዳጅ አቅርቦት እና ስርጭት መሻሻል በሀዋሳ ከተማ የትራንስፖርትና ንግድ እንቅስቃሴን ይበልጥ አሳልጧል

ሀዋሳ፤ ግንቦት 15/2018(ኢዜአ)፦ በሀዋሳ ከተማ የነዳጅ አቅርቦት  እና ስርጭት በመሻሻሉ በትራንስፖርትና በንግድ እንቅስቃሴ ላይ ተፈጥሮ የነበረው ጫና መቀረፉን የከተማዋ ንግድና ገበያ ልማት መምሪያ አስታወቀ፡፡

መንግስት በመካከለኛው ምስራቅ በተፈጠረው ችግር ምክንያት ያጋጠመውን የነዳጅ አቅርቦት ችግር መቋቋም ያስቻሉ የመፍትሄ እርምጃዎችን መተግበሩ ይታወሳል፡፡

በሀዋሳ ከተማም መንግስት የወሰዳቸውን የመፍትሄ እርምጃዎች ተከትሎ የአቅርቦት ሁኔታው ወደነበረበት ተመልሷል።

የሀዋሳ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባና የንግድና ገበያ ልማት መምሪያ ኃላፊ አገና ኔቶ እንደገለጹት፤ የነዳጅ አቅርቦት መሻሻሉ በከተማዋ የትራንስፖርትና ንግድ እንቅስቃሴ የበለጠ እንዲሳለጥ አስችሏል።


 

በከተማው በመንግስት በተቀመጠው አቅጣጫ መሠረት ነዳጅ በቁጠባ ጥቅም ላይ እንዲውል ሲደረግ መቆየቱንም  አስታውሰዋል።

በተለይም ለሕዝብ ትራንስፖርት፣ ለአምራች ኢንዱስትሪዎች እንዲሁም ሸቀጣሸቀጦችን ለሚያጓጉዙ የጭነት ተሽከርካሪዎች ቅድሚያ በመስጠት የማዳረስ ሥራ ሲሠራ እንደነበር ገልጸዋል፡፡

መንግስት ችግሩን ለመቅረፍ በወሰደው ቁርጠኛ አቋም አቅርቦቱ ወደ ነበረበት መመለሱንና በዚህም በትራንስፖርትና በንግድ እንቅስቃሴ ላይ ተጨባጭ ለውጥ መታየቱን ተናግረዋል።

መምሪያውም ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመቀናጀት የነዳጅ ስርጭቱ በአግባቡና በፍትሐዊነት እንዲዳረስ የክትትል ሥራውን አጠናክሮ መቀጠሉን ጠቁመዋል፡፡

ማደያዎች እና አሽከርካሪዎች በበኩላቸው ቀደም ሲል በነዳጅ አቅርቦት እጥረት ምክንያት በማደያዎች አካባቢ ረጅም ሰዓት ይሰለፉ እንደነበር አስታውሰው፣ አሁን ላይ ግን አቅርቦቱ ወደ ቀድሞ ሁኔታው መመለሱን ተናግረዋል፡፡


 

የሕዝብ ማመላለሻ ትራንስፖርት አሽከርካሪው ታረቀኝ ኢዩኤል ከሀዋሳ ወደ ተለያዩ ከተሞች የትራንስፖርት አገልግሎት እንደሚሰጡ ገልጸዋል።

የነዳጅ አቅርቦቱ ውስን በሆነበት ወቅት እኛም ሆንን ማኅበረሰቡ ለከፍተኛ ችግር ተዳርገን ነበር፤ ነዳጅ በሳምንት አንድ ወይም ሁለት ጊዜ ብቻ የምናገኝበት አጋጣሚ ነበር ብለዋል።

አሁን ላይ ግን ያለ ምንም እንግልት በቀላሉ ነዳጅ እያገኘን ማኅበረሰቡን በሚገባ ማገልገል ችለናል ሲሉ ገልጸዋል።


 

ሌላው በጭነት ትራንስፖርት ሰጪ ተሽከርካሪ ላይ ረዳት ሆነው እየሠሩ የሚገኙት ሲሳይ ጌጣ፤ በአብዛኛው እህልና ሸቀጣሸቀጦችን የማጓጓዝ ሥራ እንደሚሠሩ ተናግረዋል።

አሁን የነዳጅ አቅርቦቱ በመሻሻሉ መደበኛ ሥራቸውን በተሻለ ሁኔታ ማከናወን መቻላቸውን አስረድተዋል።


 

በሀዋሳ ከተማ የታፍ ነዳጅ ማደያ ሥራ አስኪያጅ ያሬድ ካሱ፤ ነዳጅ በአግባቡ እየቀረበ እያገኘን ነው፤ እኛም ለተጠቃሚዎች ፍትሐዊ በሆነ መንገድ እያደረስን ነው ብለዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም