ቀጥታ፡

ለምርጫው በስኬት መጠናቀቅ የበኩላችንን እየተወጣን ነው - ተፎካካሪ ፓርቲዎች

ባህር ዳር፤ ግንቦት 15/2018(ኢዜአ)፦ ሰባተኛው ጠቅላላ ሀገራዊ በስኬት መጠናቀቅ የበኩላቸውን ድርሻ እየተወጡ እንደሚገኙ በአማራ ክልል የሚንቀሳቀሱ የተለያዩ ተፎካካሪ ፓርቲ አመራሮች ገለጹ።

በምርጫው ለመወዳደር የተመዘገቡ ተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ ምርጫው ለሀገር አንድነትና ለሕግ የበላይነት መረጋገጥ ያለውን ፋይዳ በመገንዘብ ከዝግጅት ምዕራፍ ጀምሮ እስካሁን ተሳትፏቸውን እያጠናከሩ መጥተዋል።

መራጩ ሕዝብ በድምፁ የሚፈልገውን ፓርቲ ወደ ሥልጣን ለማምጣት የወሰደውን የምርጫ ካርድ በአግባቡ ይዞ፣ በምርጫው ዕለት በአግባቡ እንዲጠቀምበትም ፓርቲዎቹ መልእክት አስተላልፈዋል።


 

የአማራ ዴሞክራሲያዊ ኃይል ንቅናቄ (አዴሃን) ማዕከላዊ ኮሚቴ አባል ገብረመስቀል አደመ እንደገለጹት፤ ፓርቲያቸው የምርጫው ሂደት ፍትሃዊና አሳታፊ እንዲሆን የበኩሉን ድርሻ እየተወጣ ይገኛል።

ፓርቲያቸው እስካሁን ለአባላቱና ለደጋፊዎቹ የምርጫ ሕጉንና የፓርቲውን ማኒፌስቶ መሠረት በማድረግ ግንዛቤ መፍጠሩን አውስተዋል።

የሰለጠነ የፖለቲካ ትግል መገለጫው የሚፈልጉትን ፓርቲ በካርድ ወደ ሥልጣን ማምጣት መሆኑን መራጩ ሕዝብ መገንዘብ እንዳለበትም ገልጸዋል።

በዚህም መራጩ ሕዝብ ያወጣውን የምርጫ ካርድ በአግባቡ በመያዝ፣ በዕለቱ ሀገርና ሕዝብን ያሻግራል ብሎ ያመነበትን ፓርቲ እንዲመርጥ መልእክት አስተላልፈዋል።


 

የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) የሰሜን ኢትዮጵያ አስተባባሪና የአማራ ክልል የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት ሥራ አስፈጻሚ ሃይለማሪያም ብርሃኑ በበኩላቸው፤ በሕዝብ ዘንድ ቅቡልነት ያለው መንግሥት ለመመስረት ምርጫ ዋናው መሣሪያ መሆኑን ገልጸዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም