ቀጥታ፡

በኢትዮጵያና የተባበሩት ዓረብ ኢምሬቶች መካከል ያለው ሁሉን አቀፍ ስትራቴጂያዊ ትብብር እያደገ መጥቷል

አዲስ አበባ፤ ግንቦት 14/2018 (ኢዜአ)፦በኢትዮጵያና የተባበሩት ዓረብ ኢምሬቶች መካከል ያለው ሁሉን አቀፍ ስትራቴጂያዊ ትብብር እያደገ መምጣቱን በተባበሩት ዓረብ ኢምሬቶች የኢትዮጵያ አምባሳደር ጀማል በከር (ዶ/ር) ገለጹ።

በኢትዮጵያ ተግባራዊ የተደረገው የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ኢትዮጵያን ምቹ የንግድና ኢንቨስትመንት መዳረሻ ማድረጉንም ገልጸዋል።

በሀገራቱ መካከል ያለው የንግድ ልውውጥ 6 ነጥብ 1 ቢሊዮን የአሜሪካ ዶላር መድረሱም ተገልጿል።

በዱባይ የንግድ ምክር ቤት የተዘጋጀው የዱባይ - ኢትዮጵያ ቢዝነስ ትብብር ፎረም በአዲስ አበባ እየተካሄደ ነው። 


 

በተባበሩት ዓረብ ኢምሬቶች የኢትዮጵያ አምባሳደር ጀማል በከር (ዶ/ር) በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ የአፍሪካ የንግድና ኢንቨስትመንት የስበት ማዕከል ናት።

ኢትዮጵያ በቀጣናው ለኢንቨስትመንት የተመቸ ስነ ምህዳር፣ የጂኦግራፊ አቀማመጥ ለስራ ብቁ የሆነ የሰው ሀይል ያላት ምቹ የቢዝነስ መዳረሻ መሆኗን ገልጸዋል።

ኢትዮጵያ የወጣቶች ምድር የአንድ ነጥብ አራት ቢሊዮን አፍሪካውያን የገበያ መግቢያ በርና የምቹ የኢንቨስትመንት መዳረሻ መሆኗንም ገልጸዋል።

የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው ሁሉንም የንግድና ኢንቨስትመንት እንቅፋቶችን በማስወገድ ኢትዮጵያን ለንግድና ኢንቨስትመንት ምቹ ሀገር አድርጓታል ብለዋል።

የአንድ መስኮት አገልግሎት ማዕከልን ጨምሮ በተሟላ መሰረተ ልማት ፈጣንና ቀልጣፋ የንግድ አገልግሎት መስጠት የሚያስችል ሥርዓት ተዘርግቷል ብለዋል።

ኢትዮጵያ በአፍሪካ ግዙፉ የአየር መንገድ፣ የባቡርና ተሽከርካሪ የተሳለጠ የሎጂስቲክስ አገልግሎት መስጠት የሚያስችል መሰረተ ልማት መዘርጋቷን ጠቅሰዋል።

በኢትዮጵያና የተባበሩት ዓረብ ኢምሬቶች መካከል ያለው ሁሉን አቀፍ ስትራቴጂያዊ ትብብር እያደገ መሆኑን ገልጸው፣ ይህንንም የሀገራቱ መሪዎች በፅኑ መሰረት ላይ እንዲገነባ አድርገውታል ብለዋል።


 

የዱባይ ንግድ ምክር ቤት ፕሬዝዳንትና ዋና ሥራ አስፈፃሚ ሞሐመድ አሊ ራሸድ፤ ኢትዮጵያ በአፍሪካ ወሳኝ የንግድ ኢንቨስትመንትና የገበያ መዳረሻ መሆኗን ገልጸዋል።

ኢትዮጵያ ወሳኝ ስትራቴጂካዊ መልክዓምድር ያላትና በአፍሪካ ግንባር ቀደም የኢኮኖሚ ዕድገት ላይ እንደምትገኝም ተናግረዋል።

የተባበሩት ዓረብ ኢምሬቶች እና ኢትዮጵያ ያላቸው የንግድና ኢንቨስትመንት ትብብር ወደ ላቀ ደረጃ እያደገ መምጣቱንም ጠቅሰዋል።

ሁለቱ ሀገራት በንግድ፣ ኢንቨስትመንት፣ ግብርና እና መሰል መስኮች ትብብራቸው እያደገ በመምጣቱ የተባበሩት ዓረብ ኢምሬት ኩባንያዎች ኢትዮጵያን መዳረሻ እያደረጉ መሆናቸውን ገልጸዋል።

በዱባይ ከአንድ ሺህ 660 በላይ የኢትዮጵያ ኩባንያዎች በንግድ፣ ሪልስቴት፣ ሎጂስቲክስና መሰል ዘርፎች ተሰማርተው እንደሚገኙም ገልጸዋል።

በኢትዮጵያ እና የተባበሩት ዓረብ ኢምሬቶች መካከል ያለው የንግድ ልውውጥ 6 ነጥብ 1 ቢሊዮን የአሜሪካ ዶላር መድረሱን ገልጸው፤ የዛሬው ፎረምም የሁለቱን ሀገራት ኩባንያዎች ንግድና ኢንቨስትመንት ያጠናክራል ብለዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም