ቀጥታ፡

ከተለያዩ ሀገራት ጋር የተደረጉ ስምምነቶች የአየር መንገዱን ዓለም አቀፍ ተደራሽነትና ገቢ ለማስፋት ጉልህ ሚና  ይጫወታሉ

አዲስ አበባ፤ ግንቦት 12/2018(ኢዜአ)፦ከተለያዩ ሀገራት ጋር የተደረጉ የአየር አገልግሎት  ስምምነቶች  የአየር መንገዱን ዓለም አቀፍ ተደራሽነትና ገቢ በላቀ ደረጃ ለማሳደግ ጉልህ ሚና እንዳላቸው የውጭ ግንኙነትና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ገለጸ።

በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውጭ ግንኙነትና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ከተለያዩ ሀገራት ጋር በተደረጉ የአየር አገልግሎት ስምምነት ረቂቅ አዋጆች ላይ የአስረጂዎች መድረክ አካሂዷል። 


 

የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ ባንግላዲሽ፣ አንጎላ፣ ኢስዋቲኒና ሴራሊዮን በሚያደርጋቸው በረራዎች የተፈረሙ የሁለትዮሽ የአየር አገልግሎት ስምምነት እንዲሁም በኢትዮጵያና ቬትናም መካከል የዲፕሎማቲክ ወይም ኦፊሻል አገልግሎት ፓስፖርት ለያዙ ሰዎች ቪዛን ለማስቀረት የተፈረመው ስምምነት ረቂቅ አዋጆች ላይ በዝርዝር ውይይት ተደርጓል።

የቋሚ ኮሚቴው አባላትና የምክር ቤቱ የህግ ማእከል በስምምነቶቹ ፋይዳ፣ የበረራ ደህንነት መጠበቅ፣ በኢሚግሬሽን ቁጥጥር፣ የአየር መንገዶች ገንዘብ የመታገድ ችግር፣ የአየር መንገዶች የመሬት ላይ አገልግሎቶች ጋር የተያያዙ አስተያየቶችና ጥያቄዎችን አንስተዋል።

ከሀገራቱ ጋር የተደረገው ስምምነት ከኢትዮጵያ ህገ-መንግስት፣ ከሌሎች ህጎች እንዲሁም ሀገሪቱ ካፀደቀቻቸው ዓለም አቀፍ ድንጋጌዎች ጋር እንዳይጋጭ ጥንቃቄ ማድረግ እንደሚያስፈልግም ተናግረዋል።

የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ ዲማ ነጎ (ዶ/ር)፥ ረቂቅ አዋጆቹን የሀገራትን ሉዓላዊነት ባከበረ መልኩ የሀገሪቱን ደህንነት በማስጠበቅና ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነትን በማጠናከር በተለያዩ አማራጮች ሀገሪቱን ተጠቃሚ ለማድረግ ማዳበር እንደሚያስፈልግ አስገንዝበዋል።

ስምምነቶቹ የኢትዮጵያ አየር መንገድ የሚሰጠውን አገልግሎት ተወዳዳሪነት ለማላቅና የሀገሪቱን ጥቅም በማስጠበቅ ረገድ ከተለያዩ ህጎችና ዓለም አቀፍ ስምምነቶች ጋር የተጣጣመ መሆኑን ደግሞ የውይይቱ ተሳታፊዎች አስረድተዋል።


 

በኢትዮጵያ አየር መንገድ ዓለም አቀፍ ግንኙነት ተጠባባቂ ዳይሬክተር ጳውሎስ ኃይሌ፤ ከሀገራቱ ጋር የተደረጉ ስምምነቶች የአቪዬሽን ደህንነት፣ ዓለም አቀፍ ስምምነትና ብሔራዊ ጥቅምን መሰረት ያደረጉ ናቸው ብለዋል።

ስምምነቶቹ ለቱሪዝም፣ ንግድና ኢንዱስትሪዎች እድገት ጠቀሜታቸው ከፍ ያለ መሆኑን አንስተዋል።

የአየር መንገዶች ገንዘብ የመታገድ ችግር ከባለድርሻ አካላት ጋር በዲፕሎማቲክ መንገድ እየተፈታ መሆኑን ገልጸዋል።

አየር መንገዶች በተለያዩ ሀገራት የሚጠቀሟቸው የመሬት ላይ አገልግሎቶች የአየር መንገዶች አገልግሎት ብቃት ማሳያ መሆኑንና ከዓለም አቀፍ ስታንዳርዶች ጋር በተጣጣመ  መልኩ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል።

በኢትዮጵያ ሲቪል አቪዬሽን ባለስልጣን የኢኮኖሚና ሬጉሌሽን ዳይሬክተር ናርዶስ በድሉ፤ ከተለያዩ ሀገራት ጋር የተደረጉት ስምምነቶች የአየር መንገዱን ተደራሽነትና የትራፊክ መብቶችን የሚያሳድጉ እንዲሁም ተደራራቢ ቀረጥና ወጪን ለመቀነስ የሚያስችሉ መሆናቸውን ገልጸዋል።

በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የዓለም አቀፍ ህግ ጉዳዮች ዳይሬክተር ጀነራል ይበቃል ግዛው፤ ከቬትናም ጋር የዲፕሎማቲክ ወይም ኦፊሻል አገልግሎት ፓስፖርት ለያዙ ሰዎች ቪዛን ለማስቀረት የተፈረመው ስምምነት የኢትዮጵያን ሉዓላዊነትና የመወሰን ነጻነት የጠበቀ ነው ብለዋል። 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም